Saturday, 26 March 2016

በተቋማት ጥምረት አሰራር ብቅ ያለ ፈጠራ (በአሉላ ወርቁ)



የሁለተኛውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመን ለማሳካት ከተያዙት ቁልፍ ስራዎች መካከል ብቁ የሰው ሀይል ማፍራት የሚለው ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል፡፡ በእቅድ ትግበራውም 80 በመቶውን የሚሆነው በዝቅተኛና መካከለኛ ደረጃ ከቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ዘርፍ ለማፍራት አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ በዚህ አቅጣጫ መሰረትም ሰፊ ህዝባዊ መሰረት ያለው የጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፍ በምርት ጥራትና ምርታማነት በተሰጠው ልዩ ትኩረት ዘርፉን ለሚቀላቀሉ ዜጎች ከፍተኛ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል፡፡ እነዚህ ዜጎች ራሳቸውን ከመቻል አልፎው ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለሚደረገው ሽግግር የጀርባ አጥንት እንዲሆኑ ለማስቻልም የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ኢንተርፕራይዞችን በአራት የድጋፍ ማዕቀፎች ማለትም የካይዘን አቅም ግንባታ፣ የስራ ፈጠራ አቅም ግንባታ፣ የቴክኒካል ክህሎት አቅም ግንባታ እና የቴክኖሎጂ አቅም ግንባታ እንዲያገኙ የማድረግ ተግባር ይከናወናል፡፡
በዚህ መሰረትም በአዲስ አበባ በመንግስት፣ በግልና በመያድ የተቋቋሙ 336 የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ኮሌጆችና ተቋማት ከላይ በተጠቀሰው አቅጣጫ የሰው ሃይል እያመረቱ ይገኛሉ፡፡ በተለይም የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት በአራቱ የድጋፍ ማዕቀፎች በቀጥታ ከኢንተርፕራይዞች ጋር በመስራታቸው ውጤቶች መመዝገብ ችለዋል፡፡
ለውጤቱ መገኘት ደግሞ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና አሰልጣኞች በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡ በቅርብ እትሞቻችንም የአሰልጣኞች ከሚሰሩበት ተቋም ተልእኮ በመነሳት ኢንተርፕራይዞችን በሚደግፉበት ወቅት ከሚያስተውሉት ችግር በመነሳት የፈጠራ ግኝቶቻቸውን ለማበርከት መብቃታቸውን አንስተናል፡፡
የዛሬው የፈጠራ አምዳችንም የፈጠራ መነሻ ተመሳሳይ ታሪክ አለው፡፡ አሰፋ ዘለቀ ይባላል፡፡ ትውልዱ በሰሜን ሸዋ ሸኖ አካባቢ ሲሆን የመጀመሪያ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱንም እዛው በሸኖ ከተማ ተከታትሏል፡፡ የ12ኛ ክፍል ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ በቀድሞ ቴክኒክና ሙያ አሰልጣኞች ማሰልጠኛ በአሁኑ አዳማ ዩኒቨርስቲ ለአራት አመታት የማኑፋክቸሪንግ ዲፓርትመንት ስልጠናውን ተከታትሏል፡፡
ስልጠናውን አጠናቆ በ1995 ዓ.ም በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወደሚገኘው ከፍተኛ 20 ቴክኒክና ሙያ ተቋም በአሰልጣኝነት ተቀጠረ፡፡ በ2005 ዓ.ም ወደ ተግባረዕድ እስኪቀየር ድረስ ለአስር አመታት አገልግሏል፡፡ በነበረው ቆይታም 70 በመቶ የተግባር፤ 30 በመቶ የንድፈ ሀሳብ ስልጠናን በመስጠት ግዴታውን በአግባቡ እንደተወጣ ይናገራል፡፡ የፈጠራ ዝንባሌውን አስመልክቶ እንደሚናገረው ቀደም ሲል አንዳንድ ነገሮችን በቤት ውስጥ በመስራት እና የኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶችን የመጠገን ሙከራዎች ያደረግ እንደነበረ አጫውቶናል፡፡ ወደ ኮሌጅ ባቀናበት ጊዜም ተሰጦውን መሰረት አድርጎ የማኑፋክቸሪንግ ዘውግ ቀዳሚው ምርጫው አደረገ፡፡
ቀደም ብሎ እንደጠቀስነውም በሰለጠነበት መስክ ለማስልጠን ተመደበ፡፡ በተራው ወጣቶችን ማሰልጠንም ተያያዘው፡፡ አሰፋ በሰለጠነበት ዘመን እና ቀደም ብሎ ባሳለፋቸው የስራ ዘመናት አሰልጣኞች በሚገባ እንዳያሰለጥኑ ሰልጣኞችም ክህሎታቸውን እንዳያዳብሩ የሚያደርግ አንድ ማነቆ እንደነበር ይናገራል፡፡ እሱም ከፍተኛ የሆነ የግብአት ችግር ነው፡፡ አይደለም ለፈጠራ ደረጃ የሚያደርስ ሀሳብ ማንሳት ቀርቶ በተለያዩ የስልጠና ክፍሎች ለሚቀላቀሉ ሰልጣኞች ማስተማሪያ የሚሆን ግብአት አለመኖር ፈታኝ እንደነበር ያስታውሳል፡፡ ዛሬ ላይ ችግሩ ከመቀረፉ በዘለለም ጠቃሚ ግኝቶችን ለማበርከት የሚያበቃ አቅርቦት መኖሩ የተሻለ ለመስራት የሚያነሳሳ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ዘንድሮ ለስድስተኛ ጊዜ በተከናወነው ሀገር አቀፍ የፈጠራ እውቅና አስቀድሞ በ1998 ከፍተኛ 20 ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ እያለ በአነስተኛ ቦታ ላይ ለመጠቀም የሚያስችል ቀላል እና ቀልጣፋ የሽመና መስሪያ ሰርቶ ነበር፡፡ በወቅቱም በስራው ለተሰማሩ ግለሰቦች ተሰጥቶ ተሞክሮ ጥሩ ውጤት እንደተገኘበትም ከደረሰው ግብረ መልስ መረዳቱንም ያስታውሳል፡፡
ለኣዳዲስ ፈጠራዎች ትኩረትና ጊዜውን የሚሰጠው አሰፋ እንሆ በ2008 ዓ.ም በተከናወነው ሀገር አቀፍ የፈጠራ እውቅና የወርቅ ሜዳልያ ባለቤት መሆን ችሏል፡፡ መምህሩ ሶስት የፈጠራ ውጤቶች አሉት፡፡ ከነዚህ መሀከል የክብ ቶቦላሬ ማጠፊያ አንዱ ነው፡፡ መነሻ ሀሳቡ ደግሞ ከማሰልጠን ስራው ጋር ተያይዞ መሆኑ ያስገርማል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት በሚያሰለጥንበት ተግባረዕድ ተቋም ተማሪዎች ቆይታቸውን አጠናቀው ብቁ ለመሆን የተግባር ፈተና ወይም ሲኦሲ ተፈትነው ማለፉ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ታዲያ በዚህ መሀል ክብ ብረቶችን ማጠፍ አንዱ የፈተናው አካል ነበርና ይህንን የሚያደርግ መሳሪያ ከተቋምም ከገበያም መጥፋቱ ለፈጠራው መነሻ አደረገለት፡፡ በመቀጠል ችግሩን ለመፍታት ከባልደረቦቹ ጋር በመነጋገር ሀሳቡን በሚያብላለበት ቅፅበት ድጋፍ ከሚያደርጉላቸው ጥቃቅንና አነስትኛ ኢንተርፕራይዞች የተገኘ ችግር መሆኑም ፈጠራውን ለመተግበር ሌላው ገፊ ምክንያት ሆነው፡፡ በልደታ እና ቂርቆስ ክፍለ ከተሞች ከሚደግፏቸው 17 ኢንተርፕራይዞች የአብዛኞቹ ችግር የብረት ማጠፊያ መሳሪያው መሆኑ ይበልጥ እረፍት የነሳው አሰፋም ከተቋሙ በተገኙ አነስተኛ ቁሳቁሶች ችግሩን የሚፈታ መሳሪያ ሰርቷል፡፡ ራሱም እንደነገረን ለአዲስ ፈጠራው ግብአት የጠየቀው ጠቅላላ ወጪ 1200 ብር ብቻ ነው፡፡
ቀደም ሲል በችግሩ ውስጥ የነበሩት ኢንተርፕራይዞችንም የመሳሪያውን አሰራር በመውሰድ በሌሎች ተቋማት በማሰራት እና ራሳቸውም በመስራት ጥቅም ላይ ማዋላቸውን ሲናገር መላ ያበጀለትን ችግር እንደተቃለለ ይናገራል፡፡ ሁለተኛው ፈጠራውም በተመሳሳይ በእንጨት እና ቅርሳቅርስ የሚሰሩ ኢንተርፕራይዞችን ድጋፍ ሲሰጥ ያስተዋለው ክፍተት የጫረው ነው፡፡ ይህም ኢንተርፕራይዞቹ የቀርከሀ ስራዎቻቸውን በሚያመርቱበት ወቅት የማለስለስ ስራው እጅግ አድካሚና ረጅም ጊዜ መፍጀቱን በችግር ማንሳታቸው በዲፓርትመንት እንዲነጋገሩበት ምክንያት ሆነ፡፡
በተቋሙ ከባልደረቦቹ መምህራን ጋር ሀሳቦችን በመለዋወጥ ለቀርከሀም ለእንጨትም ማለስለሻ የሚያገለግል መስሪያ ማበጀት እንደቻለ አሰፋ ያስረዳል፡፡ በዚህ መሰረትም ቴክኖሎጂውን በቀጥታ መስራት ሳይሆን የአሰራሩን ሀሳብ ዝርዝር በስዕል ለኢንተርፕራይዞች መስጠቱን እና በቀርከሀ ምርት በስፋት ለሚታወቀው የደቡብ ክልል ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ እውቀቱን ማሸጋገር መቻሉም አስረድቷል፡፡ ጊዜና ጉልበትን በመቆጠብ የጥራት ደረጃን በማሻሻል የበኩሉን አስተዋፅኦ የሚያበረክት መሆኑም የታመነበት ሲሆን በሀገር ደረጃም ጥቅሙ የላቀ እንደሆነ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተረጋገጠ መሆኑን የፈጠራው ባለቤት ይናገራል፡፡
በሚያስለጥንበት ወቅት በአንድ ስራ ቦታ አብረውት ከሚሰሩት ውስጥ ወጣት በረከት ፀጋዓብ በተመሳሳይም የብዙ ፈጠራዎች ባለቤት ነው፡፡ በተቋሙ ተጋገዞ የመስራት ባህል የጠነከረ መሆኑን ይናገራል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሀሳቦችን በመደጋገፍ ለስራዎቻቸው እሙን መሆን እንደሚጠቀሙበት አስረድቷል፡፡ መስል ፈጠራዎችም ሆኑ አዳዲስ ግኝቶች መንግስት በተሰጣቸው እውቅና ልክ ተግባር ላይ ውለው የህብረተሰቡን ችግር መቅረፍ የሚቻልበትን አግባብ ማመቻቸት ቢቻል ጥሩ ነው የሚል አስተያየትም ሰጥቷል፡፡
በሶስተኛ ደረጃ የሰራው ደግሞ በቅጂ የተከናወነ ነው፡፡ ይህም ከዘመናዊ መረጃ መረብ ኢንተርኔት በመውሰድ በአንድ መሳሪያ ሩዝ፣ ጤፍና ስንዴ መዝራት የሚያስችል ነው፡፡ ያሉትን ሶስት ቀዳዳዎች በመቀያየር የተጠቀሱትን ዘሮች በመስመር መዝራት የሚያስችል ሲሆን ቀድሞ ከተሰራበት ፕላስቲክ በብረት በመተካት እና በቀላሉ መንከባለል እንዲችል የመግፊያ ጎማውን ከፍ በማድረግ እንዳሻሻለው አሰፋ ያብራራል፡፡
ቴክኖሎጂው መቶ በመቶ ተጠናቆ ወደ ተጠቃሚው ለማስተላለፍ 2500 ሺህ ብር ተተምኖለታል፡፡ ይህ ደግሞ በአሁኑ ሰአት በስፋት እየተከናወነ ላለው ግብርና እጅግ ጠቃሚ መሆኑን በመረዳት የሳይንስና ቴክሎጂ ሚኒስቴር የወርቅ ሜዳሊያ እና የስድስት ሺህ ብር ሽልማት አበርክቶለታል፡፡ ለዚህ አመርቂ አፈፃፀሙም የተግባረዕድ ተቋም የወርቅ ሽልማት አበርክቶለታል””
‹‹ሽልማት ለጥረት እውቅናን ከመስጠት አልፎ ለቀጣይም ብርታትን የሚያስታጥቅ የሞራል ግብአት ነው›› ይላል አሰፋ፡፡ በሽልማት ብቻ ሳያበቃ በዘንድሮው አመት በኢትዮ ቻይና ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋም የማስተርስ ትምህርት እድል አግኝቶ እየተከታተለ ይገኛል፡፡ ለሰሯቸው ስራዎች ሌላኛ ማበረታቻ ነው የሚለው አሰፋ ሌላም ሃለፊነት እንደተጣለበት ያምናል፡፡ ይህም በቆይታው የሚያገኘውን እውቀት ለተሻለ ፈጠራ እና የማሰልጠን አደራን ያስረከበው መሆኑን፡፡ ሀገራችን የሚያስፈልጋትን ስንልጡን የሰው ሀይል በመገንባት በግሉ ጠንክሮ እንደሚሰራ እና ፈጠራዎቹንም በተመሳሳይ ችግር ፈቺ ሆነው እንዲቀጠሉ ትጋቱን እንደሚቀጥል ምኞቱን ገልጿል፡፡
አሰፋም ‹‹ዛሬ ላይ የበርካታ ፈጠራ ባለቤቶች ማህበራዊ ችግሮቻችንን መሰረት አድርገው መፍትሄ እየለገሱ ይገኛሉ፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ በትስስር በመስራት ለሚስተዋሉ ክፍተቶች መላን ማበጀት ለዘላቂ የኢንዱስትሪ ልማት መረጋገጥ ትልቅ ሚና አለው›› ይላል፡፡
እኛም በፈጠራ አምዳችን ያስነበብነው ተሞክሮ የሚያሳየው ይህንኑ ነው፡፡ ፈጠራ ለማህበራዊ ችግሮች ምላሽ መስጠት መቻሉ መቀጠልም መበረታታትም ይገባዋል፡፡ ነገር ግን የተሰሩ ፈጠራዎች የመብዛታቸውን ያክል ለህብረተሰቡ ጥቅም ላይ የሚውሉበት እድል መክፈት አለበት መልዕክታችን ነው፡፡

Thursday, 24 March 2016

የእውቀትና የተስተካከለ የአመለካከት ትጥቅ ከስልጠናው (በብርሃኑ አምሃ)



ምንመራበት ስርአት “እንደ ዱላ ቅብብሎሽ ሩጫ” ፊተኛውና ነባሩ አመራር ሀላፊነቱን በተመሳሳይ መስመር ከበስተኋላው እግር በእግር እየተከተለው ለሚገኝ ተተኪ አመራር የሚያስተላልፍበትን አካሄድ እንደሚከተል ይታወቃል፡፡ ህዝብን የመምራት ከባድ ሃላፊነት እንደመሆኑ ተተኪውን አመራር በእውቀትና በክህሎት ማነፅ እና በተስተካከለ አመለካከት መቅረፅ ደግሞ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር ነው፡፡ ለዚህም ነው ድርጅታችን በየጊዜው ጀማሪ አመራሩ በልማታዊ ዴሞክራሲ መስመር ታንፆና የድርጅቱን ነባር እሴቶች በመውረስ የህብረተሰቡን ፍላጎትና ጥያቄ በእውቀት፣ በክህሎትና በስነ ምግባር እንዲመራ የአቅም ግንባታ ስራውን ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ የሚገኘው፡፡
የአዲስ አበባ መለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ይህ ተልእኮ የተሰጠው ተቋም ነው፡፡ ተቋሙ እስከ አሁን በአስር ዙር ከ3 ሺህ በላይ የተለያዩ ሰልጣኞችን አሰልጥኗል፡፡ ዘንድሮም የካቲት አንድ በጀመረውና ለተከታታይ 54 ቀናት በሚቆየው አምስተኛ ዙር የጀማሪ አመራሮች ስልጠና በተቋሙ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ በስልጠናውም 431 ጀማሪ አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡ እኛም ከሰልጣኞች ጋር ስልጠናውንና ከስልጠናው በኋላ ሊሰሩት ያሰቡትን በተመለከተ አነጋግረናቸው የሚከተለውን ብለውናል፡፡
ወጣት እየሩሳሌም ግዛው ከአራት ወር በፊት የካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 የድርጅት ዘርፍ ሃላፊ ሆና ከመሾሟ በፊት በህዋስና በመሰረታዊ ድርጅት አመራርነት ቆይታለች፡፡ በድርጅቱ ተቀርፀው ተግባራዊ በመደረግ ላይ ያሉ ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን ጠንቅቆ ማወቅ ላይ ክፍተት እንደነበረባት አልደበቀችንም”” በስልጠናው ላይ ግልፅ ያልሆነላትን በመጠየቅ በአንድ ለአምስት በህዋስና በቡድን ከመሰሎቿ ጋር ሀሳብ በመጋራት አሁን ላይ የተሟላ የአመራር ቁመና እየያዘች እንደምትገኝ አጫውታናለች፡፡
በተለይም በከተማችን የሚታየውን ሰፊ የመልካም አስተዳደር ችግር ለመፍታት በወረዳዋ በየሳምንቱና በየወሩ የተፈቱትንና ያልተፈቱትን በመለየት ስራዎች እየተገመገሙ እንዳሉ የጠቆመችን ወጣቷ በቀጣይም ችግሩን መፍታት ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ መሆኑን በመረዳት በእውቀትና በክህሎት ለመተጋገል የሚያስችላትን አቅም ከስልጠናው እያገኘች መሆኑን ትናገራለች፡፡
ከደቡብ ኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል እንደመጣ የነገረን ወጣት አህመድ ከድር በበኩሉ ከበፊቱም ሀገሪቱን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ያሸጋገሩ የድርጅቱን ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ለማወቅ ሰፊ ጥረት ሲያደርግ እንደቆየ ያወሳል፡፡ በድርጅቱ ላይ በነበረው እምነትና ቅን አመለካከት እንዲሁም በተሰማራበት የስራ መስክ ግንባር ቀደም ፈፃሚ በመሆኑ ነው ወደ አመራርነት የመጣው፡፡ ህብረተሰቡን በእውቀት እንዲያገለግል የተጣለበትን ሃላፊነት በብቃት ለመወጣት የሚያስችል አመላካከትን የሚቀርፅ በስነ ምግባር የሚያንፅና ክህሎቱን የሚያበለፅግ ስልጠና እየወሰደ መሆኑንም ነግሮናል፡፡
በየጊዜው የሚቀያየሩ አለማቀፋዊ ሁኔታዎችም በስልጠናው እየተዳሰሱ ይገኛሉ፡፡ በዚህም ሰልጣኞች በድርጅታችን የተዘረጋው ስርአት ለሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ ምን ያህል አዋጪና መተኪያ የሌለው መሆኑን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለመረዳት አስችሏቸዋል”” ወጣት አህመድም ይህንኑ ነው ያረጋገጠልን፡፡ በተለይም በድርጅታችን ተግባራዊ እየተደረገ ያለውና በብዙ የአለም አገሮች ዘንድ ያልተለመደው ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርአት በተለይም እንደኛ አገር ባሉ በርካታ ብሄር ብሄረሰቦች በሚኖሩባቸው ታዳጊ አገሮች ልማትና ዴሞክራሲ ተነጣጥለው መተግበር የማይታሰብ መሆኑን በምክንያታዊነት ለማስረዳት ስልጠናው በቂ እውቀት እንዳስጨበጠው ይናገራል”” ህብረተሰቡን በአግባቡ በማገልገል ለህዝቦች መብት መከበርና ለጥቅማቸው መረጋገጥ የድርጅቱ ነባር ታጋዮች የህይወት መስዋዕትነት ጭምር የከፈሉበትን የአላማ ፅናት በመያዝ ኪራይ ሰብሳቢነትን አምርሮ በመታገል የሚጠበቅበትን ለማድረግ ስልጠናው ከፍተኛ ተነሳሽነትና ግንዛቤ እንደፈጠረለትም ከንግግሩ ተረድተናል፡፡
ሰልጣኞች በቆይታቸው ሰባት ወሳኝ ኮርሶችን ይሰለጥናሉ፡፡ በተለይም ደግሞ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ እንደመሆናቸው ነፃ የሀሳብ ፍጭት በማድረግ የጠራ አመለካከት ይዘው ለመውጣት ያስችላቸዋል”” ልምድና ተሞክሮዎቻቸውንም እንዲለዋወጡ ስልጠናው አገናኝቷቸዋል፡፡ 

ወጣት ኪሮስ ገብረእግዚያብሄር ከትግራይ ክልል ነው የመጣችው፡፡ ልክ እንደሌሎቹ ሁሉ በቅርቡ ወደ አመራርነት የመጣች ግንባር ቀደም ወጣት ናት፡፡ አንዳንድ አካላት ያለበቂ መረጃና ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ወደ ጎን በማለት ድርጅቱን በእውቀት ሳይሆን በስሜት የሚተቹ አካላት እንዳሉ ስልጠናው ግልፅ አድርጎላታል፡፡ ለአብነትም በሀገራችን በሚካሄዱ ምርጫዎች በርካታ ፖለቲካ ፓርቲዎች የተለየ አማራጭ ባይዙም አማራጭ ያሉትን ለህዝቡ በማቅረብ በህዝብ ድምፅ በመሸነፍ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እየተደረገ ኢህአዴግ ወደ አውራ ፓርቲነት እየመጣ ያለበትን ሂደት “የፖለቲካ ምህዳሩ ጠቧል” በማለት መድብለ ፓርቲ የፖለቲካ ስርአት እንደማይከተል እንዴት አሳማኝ ያልሆነ ምክንያት እንደሚደረድሩ በስልጠናው በቂ የንድፈ ሃሳብ እውቀት ማግኘቷን ነግራናለች፡፡
በገበያ ጉድለት ሲገኝ ገበያውን ለመሙላት መንግስት ጣልቃ የሚገባበትን ሁኔታም በአንድ በኩል ነፃ ገበያ አይከተልም በሌላ በኩል ደግሞ የገበያ ንረት ህብረተሰቡን እያስቸገረው ነው የሚሉ እርስ በእርስ የሚጋጩ የሚመስሉ ሀሳቦች ወደዚህ ስልጠና ከመግባቷ በፊት ግራ ሲያጋቧት የነበሩ የኢኮኖሚ ሚስጢሮች ነበሩ፡፡ አሁን ግን በነዚህና በሌሎችም መሰል ሀሳቦች የበለጠ ግልፅነት ተፈጥሮላታል፡፡ የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ የበላይነት በልማታዊ አስተሳሰብ የበላይነት እንዲተካ ጀማሪ አመራሮች ጎራ ባለመደበላለቅ ለድርጅቱ ህልውና መቀጠል ከፍተኛ ተጋድሎ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አመላክታለች””
በኢትዮeያ ህዝቦች የትግል ታሪክ የኢህአዴግ ታሪክ እስከ 2002 ዓ.ም በሚለው የመጀመሪያው ኮርስ ላይ ስለድርጅቱ በርካታ የማያውቃቸውን ቁም ነገሮችና ህዝባዊነቱም ከምስረታው እንደሚጀምር መረዳቱን ደግሞ ከአማራ ክልል የመጣው ወጣት ጌታሰው ሞኝሆድ ይናገራል፡፡
በተለይም ድርጅቱ ወደ ስልጣን ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ የሚያስተላልፋቸው ወሳኝ ውሳኔዎች በአንዳንድ አካላት ተጣመው ስለሚቀርቡ በአንዳንድ አባላት ላይም ጭምር የሀሳብ መዋዥቅን ይፈጥራሉ”” ለአብነትም መሬት የህዝብና የመንግስት የጋራ ሀብት ነው የሚለው ህገ መንግስታዊ ድንጋጌ በመከተላችን አሁን ላይ በመንግስት እየተከናወኑ ያሉ የህዝብ መሰረተ ልማቶች አለምን አማለዋል”” መሬት አይሸጥም አይለወጥም በመባሉም ደሀው የህብረተሰብ ክፍል መሬቱን እየሸጠ መሬት በውስን ባለሀብቶች እጅ እንዳይገባ ፍቱን መድሀኒት ሆኗል፡፡ እውነታውና እየሆነ ያለውም ይሄ ቢሆንም አንዳንድ አካላት ግን ይህንን ማውራት አይፈልጉም፡፡ ሌላ ማደነጋገሪ መንዛት እንጂ፡፡ ወጣት ጌታሰውንም እንደዚህ ያሉ ሌሎች አስተሳሰቦች ሲፈታተኑትና ብዥታ ስለሚፈጥሩበት መርሁን አምኖ ድርጅቱን ቢቀላቀልም ለሌሎች ተንትኖ ማስረዳትና ማሰመን ይቸገር እንደነበረ አልሸሸገም፡፡ አሁን ግን በስልጠናው ሰፊ ግንዛቤ ስለጨበጠ ከስልጠናው እንደወጣም የተዛቡ አመለካከቶችን በማስተካከል ህብረተቡን በተሻለ አቅም በአመራር ስልት ለመምራትና ለማገልገል በተጠንቀቅ ላይ ነው፡፡
ከኦሮሚያ ክልል የመጣችው ፀሀይቱ አንበሴ በወሰደቻቸው አጫጭር ስልጠናዎችና በግል ራሷን ለማብቃት ባደረገችው ጥረት በመታገዝ ለአንድ አመት ያክል በአመራርነት ቆይታለች፡፡ ስልጠናው ከነበራት እውቀት ሰፊና የተተነተነ መረጃ በመስጠት ወደተሟላ የአመራር ቁመና እየወሰዳት እንደሚገኝ አስረድታለች፡፡ በአካባቢዋ የሚታዩ የመልካም አስተዳደርና ሌሎች ከአገልግሎት አሰጣጥ እንዲሁም ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር የተያያዙ ህዝቡን የሚያማርሩና ለልማት እንቅፋት የሆኑ ነገሮችን በመተጋገል ህብረተሰቡን በቅንነት ለማገልገል ቁርጠኛ አቋም መያዟን ተረድተናል፡፡
ሰልጣኞች ወደ ስልጠናው ሲገቡ ፈተና ወስደዋል”” ዋና አላማውም ሰልጣኙ በፖሊሲና ስትራቴጂዎች ላይ ያለውን እውቀት እንዲመዝን ነው፡፡ ተቋሙም የሰልጣኞች መመዘን ውጤቱን ተንትኖ ደከም ያሉትንም ምን ምን ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ለማወቅና በስልጠናው ሂደት በግብአትነት ለመጠቀም መሆኑን በአዲስ አበባ መለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ምክትል ዳይሬክተርና የአካዳሚክ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ሀርጋሞ አማሞ ይናገራሉ፡፡
ከመግቢያ ፈተናው በኋላም ሰልጣኙ እያመጣ ያለውን ለውጥ በየምዕራፍ በሚሰጡ ፈተናዎችና ግምገማዎች በሳይንሳዊ አካሄድ ለውጡ እየታየ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡
ስልጠናው የፖለቲካ ስልጠና እንደመሆኑ ዓለማው የኢትዮጵያን ህዳሴ ጉዞ የሚያስቀጥል በንድፈሃሳብ የዳበር፣ በአስተሳሰብ የጠራ፣ በአመራር አሰጣጡ የበሰል አመራር ማምረት ነው፡፡ ሰልጣኞች የድርጅቱ የረጂም ትግል ልምድና እሴቶች፣ የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመር ምንነት፣ ከዚህ መስመር የፈለቁ የሀገሪቱ ፖሊሲና ስትራቴጂዎች ፅንሰ ሀሳቡን እንዲረዱ ብቻ ሳይሆን በአመራር ስራቸው ላይ የሚገጥሟቸው የኪራይ ሰብሳቢነት፣ የመልካም አስተዳደር ችግር፣ የትምክህትና የጠባብ እንዲሁም ሌሎች የመስመሩ ፀር የሆኑ አስተሳሰቦች የጠለቀ ግንዛቤ እንዲይዙ ያደርጋል፡፡ እስካሁን ባለው የስልጠና ሂደትም በሰልጣነቹ በኩል ስልጠናውን በጥብቅ ዲስፕሊን በመከታተል ፈጣን የንድፈሃሳብ እውቀት እድገት እያሳዩ መሆናቸውን የተቋሙ ሃላፊዎች ነግረውናል፡፡ የማያቋርጥ ሃገራዊ እድገት የሚያስቀጥልና የሚያሳካ አመራር በቀጣይነት ማምረት በራሱ አንዱ የአመራር ኡደት አካልና የመተካካት ስትራቴጂው ማሳኪያ መንገድ ነው፡፡
ሰልጣኞች የሀሳብ ፍጭት በማድረግ የጠራ አመለካከት ይዘው ይወጣሉ (የቡድን ውይይት)

Wednesday, 23 March 2016

የባለሃብቱን ተሳትፎ በማጐልበት ልማቱን እናፋጥን! (በሞሰስ ግሬስ)



By Moses Grace
enkopatsion@gmail.com




አገራችን ካሏት እምቅ የልማትና የእድገት ግብዓቶች መካከል በዋነኛነት የሚጠቀሱት የመሬት ሀብታችንና የሰው ኃይላችን መሆኑን ማውሳቱ ለቀባሪው ደጋግሞ እንደማርዳት ይሆናል። ለእድገትና ለለውጥ ያለንን ራዕይ ለማሳካትና ለዘመናት ተንሰራፍቶ የቆየ ድህነታችንን ለመቀነስ እነኝህን ሀብቶች በማቀናጀት በተገቢው መንገድ መጠቀም መቻል ይኖርበታል፡፡ በመሆኑም በመንግስት በኩል ጥረት እየተደረገ ሲሆን በአገሪቱ 80 በመቶ የሚሆነው ኢንዱስትሪ በግል ባለሃብቱ መያዙከዚህ ውስጥ የውጭ ባለሃብቶች ድርሻ 10 በመቶ መሆኑ ለአገር ውስጥ ባለሃብቱ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እነዳለ አይንተኛ ማሳያ ነው፡፡

የካቲት ተለውጧል ( በዘመን ጁንዲ)




መሐል 6 ኪሎ ላይ ተገኝተናል፡፡ ነጩ የስድስት ኪሎ ሰማእታት መታሰቢያ ሓወልት ቆሞ የታሪክ ትውስታችን ይቀሰቅሳል”” ሐወልቱ ነጭ ቀለም እንዲሆን የተደረገው የተፈፀመው ግፍ በነጮች እንደተፈፀመ ለማመላከት ይሆን? የዛሬ 78 ዓመት በወርሀ የካቲት በኢጣሊያ ፋሽስት ግራዝያኒ ትእዛዝ ለሶስት ተከታታይ ቀን በተካሄደው ግፍ ነበር ከ30 ሺህ በላይ የከተማዋ ነዋሪዎች የተጨፈጨፉት፡፡ ለመታሰቢያነቱም ሐወልቱ ቆሟል፡፡
እኛም የግጥምጥሞሽ ነገር ሆነና በየካቲት ወር ወደ አከባቢው አቀናን፡፡ ከሐወልቱ ፊት ለፊት በሚገኝ አንድ ተቋም ጉዳይ አለን”” ያ ተቋም እነዛ በኢጣሊያ ፋሽስት አገዛዝ በተጨፈጨፉ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች መታሰቢያ እንዲሆን የተሰየመ ነው፡፡ የካቲት 12 ሆስፒታል!
ቅጥር ግቢው መግቢያ በር ላይ ተገኝተናል፡፡ ፈራ ተባ እያልን ወደ ፀጥታ ሃላፊው ተጠጋን፡፡ በሌሎች ተቋማት ከዚህ በፊት የነበረውን አይነት‹‹የህሙማን መጠየቂያ ሰአት ገና ነው!! አሁን መግባት አይቻልም›› የሚል ቀጭን ትዕዛዝ አዘል ምላሽ ይጠብቀን ይሆን እያልን ነበር የተጠጋነው፡፡ ሆኖም ከግምታችን በተቃራኒ የጥበቃ ባለሙያው በምጥን ፈገግታ አጅቦ ወደ ውስጥ እንድንዘልቅ ፈቀደልን፡፡ ቅጥር ግቢው ፈጣን እንቅስቃሴ ይታይበታል፡፡ የህክምና ባለሙያው፣ ታማሚው፣ አስታማሚው፣ እጩ የህክምና ተማሪዎች ከወዲያ ወዲህ ከላይ ወደታች ይርመሰመሳሉ፡፡ ለአይን ማራኪ እና ፅዱ የሆነውን የሆስፒታሉን መንገድ ይዤ መዳረሻዬን ወደ አዲሱ ዘመናዊ ህንፃ 7ኛ ፎቅ አደረግኩ፡፡ ከ7ኛ ፎቅ ቁልቁል ወደታች ስመለከት ከዚህ ቀደም የማውቀው የካቲት 12 ሆስፒታል ስለመሆኑ ጥርጣሬ እስኪያድርብኝ ድረስ በአድናቆት ተዋጥኩኝ”” ፅዱ ሰርገኞችን ለማስተናገድ የተዘጋጀ ለፎቶ የሚመረጥ ውብ የመናፈሻ ስፍራ መስሏል፡፡ ፋውንቴኑ፣ በመልክ በመልክ የተተከሉት ውብና ማራኪ አበቦች፣ በአጠቃላይ በተጠና መልኩ ተተክለው የሚታዩት በርካታ አይነት ተክሎች ልብን ያሸፍታሉ፡፡ ለአይን ይማርካሉ፣ ከፍትፍቱ ፊቱ እንዲሉ የመንፈስ ህክምናው በየካቲት ሆስፒታል ከፅዱ ቅጥር ግቢው ይጀምራል፡፡
አቶ አስራኤል አታሮ የየካቲት 12 ሆስፒታል አስተዳደርና ልማት ፕሬዝዳንት ናቸው፡፡ ሆስፒታሉ 19 አይነት የተለያዩ የህክምና ግልጋሎት እንደሚሰጥ ይገልፃሉ፡፡ ሰፊ የህክምና አገልግሎት እንዲሰጥ የሚጠበቅበት ተቋም ቢሆንም ከዚህ ቀደም ሰፊ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግርና ቅሬታ ይነሳበት እንደነበር ይገልጻሉ፡፡ በተለይም ከድንገተኛ ህክምና አገልግሎት አሰጣጥ፤ የተመላላሽ ህክምናና ከካርድ ክፍል አገልግሎት አሰጣጥ ጋር የተያያዙ ቅሬታዎች ይነሱበት ነበር ይላሉ፡፡ በቂ የሰው ሀይል አለመሟላት ጠንካራ አደረጃጀት አለመኖር፣ ችግሮቹ ስር እንዲሰዱና የመልካም አስተዳደር ቅሬታ ምንጭም እስከመሆን መድረሳቸውን ይናገራሉ፡፡
ታዲያ የዛሬ መልካም እንቅስቃሴው ከየት መጣ ስንል ጠየቅን”” ችግሮቹን ለመቅረፍም በቅድሚያ የተቋሙን የሰው ሀይል ማሳደግ ላይ ሰፊ ርብርብ እንደተደረገና 632 ብቻ የነበረውን የሰው ሀይል በእጥፍ በማሳደግ ከ1 ሺህ 200 በላይ በማድረስ በሰው ሀይሉ ላይ ለነበረው ክፍተት ቅድሚያ በመስጠት አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኝ መደረጉን ያወሳሉ፡፡
በመቀጠልም በተቋሙ 8 የለውጥ ቡድንና 115 የ1 ለ5 አደረጃጀቶችን በተጠናከረ መልኩ እንዲዋቀር መደረጉ ሌላው መፍትሄ አምጪ እርምጃ ነበር ይላሉ፡፡ በዚህም በየስራ ክፍሉ የሚነሱ ቅሬታዎችና አቤቱታዎችን በፕሮሰስ ካውንስል መድረኮች ላይ በማንሳትና መፍትሄ በማበጀት ችግሮችን ከመሰረታቸው ለመቅረፍ እንዳስቻላቸው ይናገራሉ፡፡ በዚህም በተቋሙ አገልግሎት ፈልገው የሚመጡ ህሙማንና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች የእርካታ መጠን መሻሻል እንዳሳየ ይናገራሉ፡፡ይህንንም ከጤና ቢሮና ከከተማው አስተዳደር ጋር በመሆን በተደረገ ጥናት በዘንድሮው አመት የእርካታ መጠኑ ከ85 በመቶ በላይ እንደደረሰ ተናግረዋል፡፡ ለተገኘው መሻሻልም የለውጥ ቡድኖች ትግል ቁልፍ ስፍራ እንደሚይዝ ነው የተናገሩት፡፡
‹‹በደፈናው አደረጃጀት ስለተፈጠረ ብቻ ችግር አይፈታም›› የሚሉት ፕሬዝዳንቱ ይልቁኑ ያልተፈቱ ችግሮችን በጊዜ ቅደም ተከተል በማስቀመጥ እስከ መጨረሻው ትግል እንዲካሄድበት መደረጉን ያብራራሉ፡፡ እርምጃውንም ከካርድ ክፍል ጀምሮ በማቀጣጠልና መዋቅራዊ ለውጥ በመፍጠር ካርዴ ጠፋ፤ አለአግባብ ተንገላታሁ፣ ተበደልኩ የሚሉ የተገልጋይ ቅሬታዎችን በፍጥነት መቅረፍ መቻሉን ይናገራሉ፡፡ በተጨማሪም ህክምና ፈልገው የመጡ ህሙማን ወዴት መሄድ እንዳለባቸው ጭምር ከካርድ ክፍሉ የእለት ተረኞች በቂ መረጃ የሚያገኙበት አዲስ አገልግሎት አሰጣጥ መዘርጋቱን ነው የገለፁት፡፡
ሌላው ከተመላላሽ ህክምና ጋር በተያያዘ ይነሳ የነበረውን ቅሬታና መንገላታት በየደረጃው ካሉ የህክምና ባለሙያዎች ጋር በመነጋገር መፍታታቸውን ይገልፃሉ፡፡ እኛም በሆስፒታሉ ፕሬዝንዳንት ተጀመሩ፤ ስራላይ ዋሉ የተባሉትን እውነታዎች መሬት ላይ መኖራቸውን ለማረጋገጥ ወደ ተለያዩ ክፍሎች ተዘዋውረን ቅኝት አደረግን፡፡
የሺሀረግ ጎላ በካርድ ክፍሉ ለረጅም አመታት ሰርታለች፡፡ ከዚህ በፊት በነበረው አሰራር ሁሉም አይነት ህክምናዎች አንድ ላይ ይስተናገዱ ስለነበረ ከፈጣን አገልግሎት አለመኖር ጋር ተያይዞ የህክምና ፈላጊው እሮሮ ከፍተኛ ነበረ ትላለች፡፡ አሁን ላይ የ1ለ5 ውይይቶች ተጠናክረው ወደ ተግባር መግባታቸው ለነበሩ ችግሮች መፍትሄ መስጠት እንዳስቻላቸው ትገልፃለች፡፡ በተጨማሪም የድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች ቁጥር መበራከቱ፣ የፕሮሰስ ካውንስል ላይ በነፃነት የሚደረጉ ውይይቶች እልባት አምጪ መሆናቸው በካርድ ክፍል ላይ ይነሱ የነበሩ ቅሬታና አቤቱታዎች እንዲወገዱ እንዳስቻለ ነግራናለች፡፡
ለወሊድ ክትትል ከልደታ ክፍለ ከተማ ሪፈር ይዛው እንደመጡ የነገሩን ወ/ሮ አልማዝም የካርድ ክፍሉን አገልግሎት አሰጣጥ መሻሻሉን ይመሰክራሉ፡፡ ከዚህ ቀደም የነበረው የካቲት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ አገልግሎት አሰጣጡ መሻሻሉን እንደታዘቡም ነግረውናል፡፡ ቀጣይ የእርግዝና ክትትላቸውንም እዚሁ ለመከታተል ለመውለድ ማቀዳቸውን ነው የነገሩን፡፡
የየስራ ክፍሎቹ ተናቦ መስራት የነበረውን እንግልት እና አላስፈላጊ ምልልስ አስቀርቷል፡፡ ይህ ተጠናክሮ በሌሎችም ተቋማት ሊቀጥል ይገባል ሲሉ ነው ነፍሰ ጡሯ ተጨማሪ ሀሳባቸው ያጋሩን፡፡
የሆስፒታሉ አገልግሎት አሰጣጥ፣ የባለሙያዎቹ ክትትልና ድጋፍ መደነቅን እንደፈጠረባቸው የሚገልፁት ደግሞ አቶ ለገሠ ደምሴ ናቸው፡፡ ለአንገት በላይ ህክምና ተኝተው ህክምናቸውን በመከታተል ላይ መሆናቸውን ነግረውናል፡፡ እስከ አሁን በነበራቸው ቆይታም ብዙ መልካም ጎኖችን እንደታዘቡ ነው የተናገሩት፡፡ አጎታቸውን እያስታመሙ ያገኘናቸው ወ/ሮ አስናቀች ወዳጆም የአቶ ለገሠን ሀሳብና አስተያየት ያጠናክራሉ፡፡ ‹‹ይህ ለውጥ የአጭር ጊዜ ብቻ መሆን የለበትም ወደፊትም ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል፡፡›› ነው ያሉን፡፡
አሁን ላይ ያለው ቅሬታና አቤቱታ ምን ላይ ደርሷል? ተቋሙስ እንዴት ነው ቅሬታና አቤቱታን በየጊዜው የሚመለከተው? ስንል ቀጣይ ቅኝት ያደረግነው ወደ ተቋሙ የደንበኞች ቅሬታ ሰሚ ክፍል ነበር፡፡ የክፍሉ አስተባባሪ ሃላፊ አቶ አብርሃም ድርባ ከዚህ ቀደም ከተለያዩ ባለጉዳዮች በየእለቱ በርካታ ቅሬታዎች ይመጡ እንደነበር፤በተለይም በካርድ፣ በላቦራቶሪና በመድሃኒት ክፍል እንዲሁም በድንገተኛ ክፍል ላይ የነበረው ቅሬታ መጠኑ ሰፊ እንደነበር ያወሳሉ፡፡ በስራ ክፍሎቹ ላይ ይነሱ የነበሩ ተደጋጋሚ ቅሬታዎች አሁን ላይ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ መፊታታቸውን ተናግረዋል፡፡
የካርድ ክፍሉ በተለየ አሰራር እንዲዋቀር መደረጉ የሚጠፋ ካርድ እንዳይኖር፣ ካርድ ወደሌላ ክፍል የሚወስደውም ሆነ የሚቀበለው አካል በፊርማው የተቀበለውን ካርድ ብዛትና አይነት እንዲያረጋገጥ በማድረግና በየጊዜው ከባለጉዳዩ የሚሰጡ አስተያየቶችን በመሰብሰብ ቅሬታ ለተነሳባት ጉዳይ አፋጣኝ እልባት እንዲያገኝ ለማስቻል በተሰራው ስራ ለውጥ መገኘቱን ይገልፃሉ፡፡
በሆስፒታሉ የፕላስቲክና የአጥንት ህክምና ዋርድ ሃላፊና ፕሮፌሽናል ነርስ የሆኑት አቶ ሠለሞን አሰፋ በበኩላቸው የቅሬታና አቤቱታ ሰሚ ኮሚቴዎች መዋቀራቸውና ባለጉዳዩን የሚያጋጥሙ ችግሮች ያለምንም ውጣ ውረድ በኮሚቴው አፋጣኝ እልባት እንዲያገኙ እየተደረገበት ያለው አሰራር በተቋሙ የሚያጋጥሙ ችግሮች ስር ሳይሰዱ በቀላሉ እንዲፈቱ አስችሏል ይላሉ፡፡
በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ብቻ የሚስተዋለውን ችግር ሳይሆን የተቋሙን የግዥ ስርአት ህጋዊ መልክ በማስያዝ እንዲሁም በድንገተኛ ህክምና ላይ የነበረውን የአገልግሎት አሰጣጥ ውስንነት በማስቀረት አሁን ላይ ያለ ገደብ ለድንገተኛ ህክምና የመጣውን ህክምና ፈላጊ ማስተናገድ መጀመሩን ይናገራል፡፡
ዛሬ የካቲት በጨቅላ ህፃናትና እናቶች ህክምና እንዲሁም የፕላስቲክ ሰርጀሪን ጨምሮ ከፍተኛ የእሳት አደጋ ተጎጂ የሆኑ ህሙማንን ለረጅም ጊዜ አስተኝቶ በማከምና ድነው ማህበረሰቡን እንዲቀላቀሉ በማድረግ ረገድ እያደረገ ያለው ሰብአዊ ተግባር አንቱታን እያጎናፀፈው ይገኛል በማለት ተጨማሪ አስተያየታቸው ሰጥተዋል፡፡
ወቅታዊ መረጃዎች እንደሚያመላክቱትና እኛም በአይናችን እንደተመለከትነው በከተማ ውስጥ ያሉ የሪፈራል ሆስፒታሎችን ጨምሮ የካቲት 12 ድንገተኛ ህክምናን በማስተናገድ ግምባር ቀደም ሚናውን በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡
በ2007 ዓ.ም የአዲስ አበባ ጤና ጥበቃ ቢሮ በሰራው የደንበኞች እርካታ ምዘናም በተቋሙ አገልግሎት አሰጣጥ የደንበኞች እርካታ ከ85 በመቶ በላይ መድረሱን ነው በጥናቱ ያረጋገጠው፡፡ ይህ ማለት ግን የመጨረሻው የአገልግሎት አሰጣጥና ደረጃ ላይ ደርሷል ማለት አይደለም፡፡ አሁንም ተቋሙ የጀመረውን መልካም ጅማሮ አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል፡፡ ህዝብ ደረጃ ሲሰጥ፤ ህዝብ ሲመሰክር ለበለጠ ውጤት እንዲተጋ ተጨማሪ የሞራል ስንቅ ይሆናልና የካቲቶች በርቱ መልዕክታችን ነው፡፡
በማያባራ ለውጥ ላይ ያለ ተቋም
ቀጣዩ ጉዞአችንን ያደረግነው ወደ ጃንሜዳ ጤና ጣቢያ ነው፡፡ ሀገራችን ከሁለት አስርት አመታት በፊት የ153 ጤና ጣቢያዎችና ከ70 የማይበልጡ ሆስፒታሎች ብቻ ነበሩዋት፡፡ ዛሬ ላይ ግን 3 ሺህ 500 ጤና ጣቢያዎች፣ 16 ሺህ 250 ጤና ኬላዎችና 350 ሆስፒታሎች ተገንብተው አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ”” ከ39 ሺህ በላይ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችም ለጤና ፖሊሲያችን ስኬትና ተግባራዊነት ጉልህ ሚና በመጫወት ላይ ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ ጤና ጣቢያዎች አንዱ የጃን ሜዳው ጤና ጣቢያ ነው፡፡ ብዙዎች በማያቋርጥ ለውጥ ላይ ያለ ተቋም በማለት ያሞካሹታል፡፡
ጤና ጣቢያው በአራዳ ክፍለ ከተማ በሰሜን ወረዳ 10 እንዲሁም በደቡብ ወረዳ 7 በምዕራብ ደግሞ ወረዳ 9 ያዋስኑታል”” ለ28 ሺህ 922 የወረዳው ነዋሪዎች ዘርፈ ብዙ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ በ5000 ካሬ ቦታ ላይ የተገነባ ባለአራት ፎቅ ህንፃ ነው፡፡ የህክምና ጤና ማጎልበትና በሽታ መከላከልን ጨምሮ በአራት የስራ ሂደቶች በመመራት የተደራጀና የተጠናከረ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ ከቅድመ ወሊድ እስከ ድህረ ወሊድ አገልግሎት፣ የሳንባ ነቀርሳ ህክምና፤ የኤች.አይ.ቪ ክትትል እንዲሁም የህፃናት ህክምና ግልጋሎት ይሰጣል፡፡
መንግስት የህብረተሰቡን የጤና ፍላጎት ተደራሽ ባደረገ መልኩ በከተማችን ሰፊ ስራዎችን በማከናወን ውጤታማ ስራ እየሰራ መሆኑን ማሳያ ሊሆን የሚችል ተቋም ነው፡፡ በከፍተኛ ወጪ የተገነባው ይህ ጤና ጣቢያ አገልግሎት መስጠት ከጀመረ 3 አመታትን አስቆጥሯል”” በክፍለ ከተማው ካሉ ግዙፍ ሆስፒታሎች በተጨማሪ ከተገነቡ 8 ዘመናዊ የጤና ጣቢያዎች መካከል አንዱ ነው፡፡
ለአይን የሚማርክ ሰፊና ፅዳቱ የተጠበቀ ቅጥር ግቢን በውስጡ ይዟል፡፡ በ128 ሰራተኞች የተዋቀረው ጤና ተቋሙ 54 የጤና ባለሙያና የድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች አሉት፡፡ ከዚህ ቀደም ከአገልግሎት ተደራሽነት ጋር በተያያዘ ቅሬታ ይነሳበት እንደነበር አቶ ጋሻው አያሌው የጃን ሜዳ ጤና ጣቢያ ሜዲካል ዳይሬክተር ይናገራሉ፡፡ በካርድና በድንገተኛ ክፍል ላይም የነበረው የአገልግሎት ተደራሽነት ቅሬታ የነበረበትና የደንበኞችን ፍላጎት መሰረት ያላደረገ ነበር ይላሉ”” ይህም ለከፍተኛ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ዳርጓቸው እንደነበረ ነው የገለፁት፡፡
በመሆኑም የዚህ ችግር ዋና መፍትሄ የጤና ሰራዊት በተቋሙ መገንባት መሆኑ መግባባት ተያዘበት፡፡ 8 ሞዴል የ1 ለ5 አደረጃጀቶችን ያቀፈ 20 የ1 ለ5፣ 1 የሴቶች ፎረም እና 4 ሞዴል የሆኑ የለውጥቡድን አደረጃጀቶችን አዋቅሮ አፋጣኝ ምላሽ መስጠት ጊዜ ሊሰጠው የማይገባ ተግባር መሆኑን በማመን ወደ ስራ ገቡ፡፡ የለውጥ ቡድኖችም መልሰው ተደራጁ፡፡ በለውጥ ቡድን አደረጃጀቶቹ በመታገዝም ችግሮችን በፕሮሰስ ካውንስል ከማኔጅመንቱና ከሰራተኛው ጋር በመፍታት ከዚህ ቀደም ለነበሩ ችግሮች ምላሽ መስጠት ቻሉ፡፡ ቀደም ሲል የነበረውን የአደረጃጀትና የተደራሽነት ችግር ለመቅረፍም የአንድ መስኮት አገልግሎት አሰጣጥን እውን ማድረግ ቻሉ፡፡ ከካርድ ክፍል ጀምሮም የአለም የጤና ድርጅት መስፈርትን ተግባራዊ በማድረገ የደንበኞች መጉላላትን፣ መመላለስን በማስቀረት አሰራሩን በሙሉ ወደ ቴክኖሎጂ በማሸጋገር ተስፋ ሰጪውን ጅማሮ ይበልጥ በተሻለ አደረጃጀት አፋጠኑት፡፡ በመቀጠልም ምቹ ያልነበረውን የድንገተኛ ክፍልም ለደንበኞች አመቺ ወደ ሆነው ወደ በር አካባቢ በማምጣት ለድንገተኛ ታካሚው ምቹ ሁኔታን ፈጠሩለት፡፡
የለውጥ ሂደቱን በዚህ ያላበቃው ተቋሙ የላብራቶሪ አደረጃጀቱንም ችግር በመቅረፍ በጊዜ በጥራት በመስራት ደረጃውን የጠበቀ የላብራቶሪ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ ይህም የላብራቶሪ አገልግሎቱን ለተገልጋዩና ለባለሙያው ምቹ እንዲሆን ከማድረግ ይጀምራል”” በዋናነትም ለላብራቶሪ ስራ የሚያስፈልጉ ግብአቶችን በመጠንም በአይነትም በማሟላት አንድ አለ፡፡ ይህም ያለምንም መቆራረጥ የተሟላ ዘመናዊ የላብራቶሪ አገልግሎት እንዲሰጥ አስችሎታል”” በቅርቡም በላብራቶሪ አገልግሎት ከአዲስ ከተማው ጤና ጣቢያ ቀጥሎ በከተማችን ሁለተኛው ባለ 5 ኮኮብ ደረጃ ላይ የደረሰ ተቋም ሊያደረገው የሚያስችለውን ራዕይ የሰነቀ ቀልጣፋ የላብራቶሪ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡
በዚህ ብቻ ያልቆመው ጤና ጣቢያው የለውጥ ማዕበሉንም ፋርማሲ ክፍል ድረስ አደረሰው፡፡ ያጋጥመው የነበረውን የመድሃኒት አቅርቦት ችግር ከመድሃኒት አቅርቦትና አስተዳደር ኤጀንሲ ጋር በጥምረት በመቅረፍ የ24 ሰዓት የተሟላ የመድሃኒት ሽያጭ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ በዚህም የደንበኞች እርካታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል፡፡ ከአቅም በላይ በሆነ የአቅርቦት ችግር ካልሆነ በቀር ደንበኞች መጥተው የማያገኙት የመድሃኒት አይነት እንደሌለ ፋርማሲስት ትዕግስት የሻኖ ትናገራለች፡፡ ይህም የህሙማንን ውጣ ውረድ በእጅጉ ማስቀረቱን ነው የገለፀችው፡፡
ጤና ጣቢያው ለሰራተኞች ምቹ የስራ አካባቢንም ፈጥሯል፡፡ የራሱ ዘመናዊ የጤና ነክ ሳይንስና ምርምርን ያካተቱ መፅሃፍትን የያዘ ዘመናዊ ቤተመፅሃፍት አለው፡፡ ከሁሉም በላይ በጥቂት የግልና የመንግስት ጤና ተቋማት የሚገኘውን የዶፕላር ማሽን አስገብቷል”” ማሽኑ አንድ እናት ከመውለዷ በፊት ፅንሱ ያለበትን አጠቃላይ የጤንነት ሁኔታ፣ የልብ ትርታ ጤናማነት ለመከታተል የሚረዳ ማሽን ነው፡፡ በተጨማሪም ፅንሱ ከመወለዱ በፊት ሊያጋጥሙ የሚችሉትን የጤና ስጋቶች አስቀድሞ ለመከላከል የሚረዳ ነው፡፡
ለእናቶች የወሊድ ክትትል የሚሆንም በሚገባ የተደራጀ ከብክለት ነፃ የሆነ የእናቶች ወሊድ መቆጣጠሪያ ክፍል አለው፡፡ በተቋሙ ለወለዱ እናቶች የጤና ጣቢያው ማህበረሰብ የሚያደርገው ቤተሰባዊ እንክብካቤም ለየት ያደርገዋል፡፡ እናቶች ከመውለጃ ጊዜያቸው መቃረቢያ ጀምሮ ወልደው ወደቤታቸው እስኪመረሱ ድረስ አስፈላጊውን ግብአት በማሟላት ቡና፣ ሻይ በማፍላት በቤታቸው ያሉ ያህል ስሜት እንዲፈጠርባቸው ያደርጋል፡፡
ተቋሙ በሚሰጠው አገልግሎት የህብረተሰቡ እርካታ ከጊዜ ወደ ጊዜ ጨምሯል፡፡ ከአጎራባች ክፍለ ከተሞች ጭምር መጥተው የሚታከሙ ህሙማን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጨምር እንዳደረገው የምትገልፀው አፀደ ብርሃኔ ናት፡፡ ከየካ ክፍለ ከተማ ነው ለወሊድ ክትትል የመጣሁት የምትለው አፀደ ከካርድ ክፍል ጀምሮ ያለው ፈጣን አገልግሎት አሰጣጥና እንክብካቤ በራሱ የመንፈስ እርካታ ነው ትላለች፡፡ ተቋሙም የደንበኞችን እርካታ በተመለከተ መመሪያው በሚያዘው መሰረት በ6 ወር ብቻ የነበረውን የደንበኞች እርካታ ልኬት በየ 3 ወር ጊዜ ውስጥ በመለካት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም በአሁኑ ሰአት የደንበኞች እርካታ 93 በመቶ ያህል መድረሱን ነው የጤና ጣቢያው ሜዲካል ዳይሬክተር የገለፁልን፡፡
እኛም እዛው ተገኝተን የታዘብነው ይህንን ሀቅ ነው፡፡ የጤና ጣቢያው ውስጣዊ አደረጃጀት ልዩ ነው፡፡ የአመራሩና የፈፃሚው መልካም ግንኙነትም ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ በማያባራ የለውጥ ሂደት ውስጥ ያለው ጃንሜዳ በቅርቡ የባለ 3 ፎቅ የፋርማሲ አገልግሎት ብቻ የሚሰጥ ህንፃ ከክፍለ ከተማው ጤና ጽ/ቤት እና ከከተማው ጤና ቢሮ ጋር በመሆን ለመገንባት ቅድመ ሁኔታዎችን አጠናቋል፡፡ ግንባታውም በመጪዎቹ አምስት ወራት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ነው ዳይሬክተሩ የገለፁት፡፡ ጃን ሜዳዎች ተቋማዊ የአሰራር ለውጦችን በመጠቀም ወደ ሞዴል ተቋምነት ደረጃ ደርሰዋል፡፡ ይህ ውጤት የሁሉም የተቋሙ ማህበረሰብ ልፋት ነው፡፡ ጃን ሜዳዎችን በርቱ ማለት እንወዳለን፡፡ ወገንን ከማገለግል በላይ የሚያስደስት ምንም የለም ብለናል፡፡ አሁንም ያሉ መልካም ተሞክሮዎችን በማስፋት ወደፊትም ተጠናክሮ ከዚህ የበለጠ መጓዝ ይገባል፡፡ ደግሞም ይቻላል”” የዛሬ ድልና ስኬት ነገን እንዳያዘናጋችሁ አደራ እንላለን፡፡
የኮልፌው አምባሳደር
የጉዞአችን መጨረሻ ወደሆነው ኮልፌ ጤና ጣቢያ አቅንተናል”” በክፍለ ከተማው ከሚገኙ 11 ጤና ጣቢያዎች መካከል አንዱ የሆነው የኮልፌ ጤና ጣቢያ በክፍለ ከተማው ወረዳ 10 አጠና ተራ አካባቢ ይገኛል፡፡ አዋሳኝ የኦሮሚያ ዞንን አዋሳኝ ክፍለ ከተሞችና አጠቃላይ የአካባቢው ነዋሪዎችን ጨምሮ ከ61 ሺህ በላይ ለሆኑ ነዋሪዎች አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ እዚህም የጤና ሰራዊቱ ዋና የአገልግሎቱ አንቀሳቃሽ ሞተር ነው፡፡ ሰራዊቱ በ29 የ1 ለ5፤ በ2 የለውጥ ቡድን አደረጃጀትና በአንድ የፕሮሰስ ካውንስል ስራውን በየጊዜው ይመራል ይገመግማል፡፡ ጤና ጣቢያው ለችግሮች አፋጣኝ እልባትና መፍትሄ በማበጀት መልካም ስምን ገንብቷል፡፡ ሰኞ፣ ሐሙስ እና አርብ የአደረጃጀቶቹ የግንኙነት፣ የስራ አፈፃፀም ግምገማ የሚካሄድባቸውና የቀጣይ ስራ እቅድ የሚተለምባቸው ጊዜያት ናቸው ያሉን ሲስተር ጥላዬ ዘዋለ በጤና ጣቢያው የበሽታ መከላከል የስራ ሂደት መሪ ናቸው”” በአደረጃጀቶቹ የግንኙነት ወቅት ያጋጠሙ ችግሮች መፍትሄ ያገኛሉ፡፡ የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ ፈፃሚዎችና የጤና ጣቢያው ማህበረሰብ አባላት እውቅና ይሰጣል፡፡ በዚህም ጥሩ የስራ ተነሳሽነትና የስራ አካባቢ መፈጠሩን ይናገራሉ፡፡
ጤና ጣቢያው በቀዶ ህክምና መዋለድ፣ በማህፀን ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና በ8 ተመላላሽ የህክምና አገልግሎት መስጫዎች ልዩ፤ ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ በተጨማሪም በጤና ማጎልበትና በሽታ መከላከል ዋና የስራ ሂደት ውስጥ ከቤተሰብ ምጣኔ ጀምሮ እስከ ፀረ ኤች.አይ.ቪ /ኤድስ/ ህክምናና የምክር አገልግሎት ድረስ ላሉ 14 አይነት የህክምና አይነቶች አገልግሎት ይሰጣል፡፡
ከዚህ ቀደም ጤና ጣቢያው ለጳውሎስ አጠቃላይ እስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሪፈር ይፅፍባቸው የነበሩ የቀዶ ጥገናና በምጥ መርፌ የማዋለድ አገልግሎት በራሱ መስጠት በመቻሉ የእናቶችን ውጣ ውረድ ቀንሷል፡፡ ይህ ተግባሩም በመዲናው ውስጥ ካሉ የመንግስት ጤና ጣቢያዎች መካከል ተመራጭ እንዳደረገው የማዋለጃ ኬዝ ቲም ሃላፊው ወጣት ዳዊት ንቁ ይገልፃል፡፡ በወር እስከ 240 የሚደርሱ እናቶችም ይህንን አገልግሎት በማግኘት ላይ መሆናቸው ከተቋሙ ያኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ወ/ሮ ቤተልሄም አክሊሉ እና ወ/ሮ ከድጃ ብርሃኑ የጤና ጣቢያው መልካም አገልግሎት ምስክሮች ናቸው፡፡ በእለቱ በጤና ጣቢያው ያገኘናቸው ሁለቱ እንስቶች ለስነተዋልዶ ጤና ክትትልና ስለ ጤናማ አመጋገብ ትምህርት ለመውሰድ መምጣታቸውን ነግረውናል፡፡ ከዚህ ቀደምም በዚሁ ጤና ተቋም ወልደው ስመዋል”” ዛሬም ጤናን በተመለከተ ከተቋሙ ጋር ያላቸው ቁርኝት ይበልጥኑ ተጠናክሯል፡፡ ስለ ስነተዋልዶና ጤናማ አመጋገብ ያላቸው እውቀትም መጨመሩን ይገልፃሉ፡፡
ብልህ ወንድም በአስተምህሮው ይሳተፋል፡፡ ወጣት ጌታቸው እንዳለን ያገኘነው በጤና ጣቢያው ባለቤቱን ለህክምና ይዞ መጥቶ ነው፡፡ ከወረዳ 13 ዊንጌት አካባቢ፡፡ የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ ይበል የሚያሰኝ ነው ሲል ያሞካሻል፡፡ ከተጠቃሚው ቁጥር ጋር ተያይዞ ያለውን መጨናነቅ ግን የሚመለከተው አካል ቢያስብበት መልካም ነው ሲል ተጨማሪ ሀሳቡን ሰጥቷል፡፡
ቀጣዩ ጉዛችንን ወደ ጤና ጣቢያው መለስተኛ ቀዶ ጥገና፣ የግርዛት አገልግሎት ወደሚሰጥበት ክፍል አድርገናል፡፡ በክፍሉ ትርፉ ጣቶችን የማስወገድ፣ በሰውነት ላይ የሚበቅሉ በአድ ነገሮችን በመለስተኛ ቀዶ ጥገና ከሰውነት ማውጣት፤ እባጮችን በዘመናዊ ህክምና የማስወገድ አገልግሎት እንደሚሰጡ ነው የጤና ባለሙያው አቶ ዳዊት ላቀው የገለፁት፡፡ የጤና ጣቢያው ደንበኞች በግል ሆስፒታሎች በከፍተኛ ዋጋ የሚያገኛቸውን ግልጋሎቶች እዚህ እስከ 90 ብር ብቻ በመክፈል ያገኛሉ ይላሉ፡፡
የጤና ጣቢያው መልካም ተሞክሮ በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ ጤና ጣቢያው በከተማችን የመድሃኒት ዝውውርን ኦዲት ትግበራ ከ3 አመታት በፊት ተግባራዊ በማድረጉም ለሌሎች በአርአያነት እንዲነሳ እንዳደረገው የፋርማሲ ክፍል ሃላፊው አቶ ሙሉጌታ ተሾመ ይገልፃል፡፡ ይህም እያንዳንዱ መድሃኒት ለተገልጋዩ እንዴት እንደደረሰ ከማሳየቱ በላይ የአንድ የመስኮት አገልግሎትን ዘመናዊ በማድረግ ህሙማን ስለሚጠቀሙት መድሃኒት ጠቀሜታና ተያያዥ የጎንዮሽ ጉዳት በቂ መረጃ እንዲኖራቸው በማሳወቅ ረገድ ብዙ ርቀት በመጓዝ ላይ ነው፡፡ በቆይታችን እንደታዘብነው የኮልፌ ጤና ጣቢያ አመራሮችና ፈፃሚዎች እያደረጉት ያለው ዘርፈ ብዙ የለውጥ ትግበራ የተሻለ ገፅታን መገንባት አስችሏቸዋል፡፡ በርቱ ጠንካራ ጎናችሁ እስከመጨረሻው ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል እንላለን፡፡
እኛም ከብዙ በጥቂቱ በየተቋማቱ ዞረን የቃኘነውን መልካም ተሞክሮ ለእናንተ ለአንባቢያን አቀረብን፡፡ ተቋማቱን በርቱ እያልን ሌሎች በአገልግሎት አሰጣጥና መልካም አስተዳደር ወደኋላ የቀሩ ተቋማት ቢሮዎችና ሴክተር መስሪያ ቤቶች የእነዚህን ግምባር ቀደም የጤና ተቋማት ልምድና ተሞክሮን ቢቀስሙ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብዙ ታተርፋላችሁ እንላለን፡፡ ጤና ይስጥልን፡፡