Tuesday, 17 May 2016

የከተማችን የነገ ተስፋ የግንቦት ፍሬዎች!




ከተወሰኑ አመታት በኋላ ኢንዱስትሪ መር የኢኮኖሚ ስርአት እንደምንከተል እሙን ነው፡፡ ኢንዱስትሪያዊነት የአንድ ሀገር ህዝብ ሁሉን አቀፍ የህይወት ለውጥ ነው፡፡ በመሆኑም በየጊዜው እየተሻሻለ የሚመጣ ማህበረሰባዊ እድገት እንጂ በአዋጅ የሚነገር ስርአት አይደለም፡፡ ሁሉንም ነገር በእቅድ ስለምንፈፅም ኢንዱስትሪው የመሪነቱን ቦታ ሙሉ በሙሉ የሚረከብበት ጊዜ በስትራቴጂዎቻችን መመላከቱ ይታወቃል፡፡
ኢንዱስትሪው መሪ የመሆኑ ሂደት ከነጉድለቱም ቢሆን መንግስት በያዘው አቅጣጫ መሰረት እየሄደ ይገኛል፡፡ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ በጨርቃ ጨርቅ፣ ብረታ ብረት፣ እንጨት ስራ ወዘተ ጅምር ለውጦች እየተመዘገቡ ነው፡፡ በገጠርና በከተማ በፍጥነት እያደገ የሚገኘው የመንገድ አውታር፣ የአገልግሎት ዘርፍ ግስጋሴ፣ መዲናችን ጨምሮ ሌሎች ትናንሽ ከተሞችንም ፈጣን እድገት እንዲያስመዘግቡና በምርቶቻቸው ላይ እሴት ጨምሮ ወደመላክ የተሸጋገሩ ኢንዱስትሪያሊስቶች ብቅ ብቅ ብለዋል፡፡
በከተሞች በርካታ ዜጎችን የሀብት ባለቤት እያደረገ የሚገኘው ጥቃቅንና አነስተኛ ልማት ኢንተርፕራይዝ ደግሞ የኢንዱስትሪ ሽግግሩን እያፋጠነው ይገኛል፡፡ ከምንም ተነስተው ራሳቸውን ጠቅመው ለሌሎችም የስራ እድል እየፈጠሩ የሚገኙና በህዳሴያችንም በየጊዜው ከአንባቢዎቻችን ያስተዋወቅናቸው በርካታ አንቀሳቃሾች ለዚህ ማሳያ ናቸው፡፡ በተስፋ መቁረጥ ስሜት ገና ከጅምሩ የሚበተኑ አንዳንድ አንቀሳቃሾች ዛሬም ባይጠፋም ዘርፍ ግን በርካታ ሴቶችና ወጣቶች ወደ ሀብት ማማ የሚወጡበት መንገድ መሆኑን ቀጥሏል፡፡ እኛም በአንድ አመት ውስጥ ስኬታማ ስራዎችን በማከናወን በዘርፉ ውጤታማ የሆኑ እንስቶችን የስራ እንቅስቃሴ ቃኝተን ለሌላው ተሞክሯቸውን እንዲያካፍሉ በዚህ መልኩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡
እንስቶቹ የስራ ቦታቸውና መኖሪያቸው በጉለሌ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ነው፡፡ በ2007 ዓ.ም በጥቃቅንና አነስተኛ ከመደራጀታቸው በፊት ተባራሪ ስራ የሚሰሩና ከፊሎቹም ያለምንም ስራ የቆዩ ናቸው፡፡ እርስ በእርሳቸው ይተዋወቁ ስለነበር ቋሚ ሀብት ለማፍራት በጋራ ለመስራት ወሰኑ፡፡ ለዚህም በጥቃቅንና አነስተኛ መደራጀትን ቀዳሚ ምርጫቸው በማድረግ ዘርፉን ሀ ብለው ተቀላቀሉ፡፡
በ2007 ዓ.ም ሲደራጁም ስምንት እንስቶችና ሁለት ወንዶች በመሆን “ሸዋዬ አልማዝና ጓደኞቻቸው ብረታ ብረት የህብረት ሽርክና ማህበር” በሚል በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ጥቃቅንና አነስተኛ ጽ/ቤት ስር ተደራጁ፡፡ የስራ ተነሳሽነትና ዝግጁነት እንጂ እውቀቱ ስላልነበራቸው ሽሮ ሜዳ ቴክኒክና ሙያ ከንድፈ ሀሳብ እስከ ተግባር ስልጠና እንዲያገኙ በማድረጉ አቅም ፈጠረላቸው”” ከመንግስት ባገኙት 42 ሺህ ብር የገንዘብ ብድር ለስራቸው የሚያስፈልጋቸውን ቁሳቁሶች ማሟላትም ቻሉ፡፡ በብረታ ብረት ስራ የተደራጁት እንስቶች የድምፅ ብክለት እንዳይኖር ታስቦ ይመስላል ከመኖሪያ ሰፈር ወጣ ያለና ለስራ ምቹ የሆነ ሼድ ለማግኘትም ጊዜ እንዳልፈጀባቸውም የማህበሩ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሸዋዬ በርሽ አጫውተውናል፡፡
በተደረገላቸው የቴክኖሎጂ ድጋፍም ተደራራቢ የብረት አልጋዎችን፣ የተለያዩ በሮችንና መስኮቶችን፣ የሽንኩርት መፍጫ ማሽን፣ የኤሌክትሪክ ምድጃዎችን፣ ምጣድና የፍራፍሬ መጭመቂያ ማሽኖችን እንደሚያመርቱና በከተማችን በስፋት ያልተለመደውን የተለያዩ ማሽኖችን ሞተር ጥገናም በጥራት እየሰሩ እንደሚገኙም በማምረቻ ቦታቸው ላይ ተገኝተን አረጋግጠናል፡፡
የብረታ ብረት ስራን ከአባታቸው እንደወረሱት የሚናገሩት ወይዘሮ ሸዋዬ በተለይም የተለያዩ ማሽኖች ሞተር ሲቃጠሉና ሲበላሹ በአዲስ መልኩ የመስራቱን ሙያ ተቀብሮ እንዳይቀር በመንግስት የተፈጠረላቸውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅመው እንዲሰሩ በማድረጉ አመስግነው አይጠግቡም፡፡ በልምድና በስልጠና ያዳበሩትን ሙያ ለስራ ባልደረቦቻቸው በማካፈል ተባብረው በመስራት ድህነትን ድል እየነሱ ይገኛሉ፡፡ ከመደራጀታቸው በፊት ቋሚ ስራ እንዳልነበራቸው የሚናገሩት እንስቷ አሁን ላይ ማህበራቸው የተበደረውን ብድር መልሰው ተጨማሪ 80 ሺህ ብር ብድር ማግኘታቸውንና ስራቸውም በተጠቃሚው ዘንድ “በጥቃቅንና አነስተኛ እንደዚህ አይነት እቃ ይመረታል ወይ?” እያስባለ እንደሚገኝና የዘርፍን ስኬታማነት እያስመሰከረ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡
ህብረተሰቡ በሺዎች ብር አፍስሶ የገዛው ማሽን ሞተር ሲበላሽበት አዲስ ከመግዛት አስጠግኖ እንዲጠቀምበት ማድረጋቸው እንደሚያስደስታቸው የገለፁት እንስቷ ከጥገና በኋላ የሁለት አመት ዋስትና እንደሚሰጡም ነግረውናል፡፡ በዚህም ደንበኞቻቸውን ይበልጥ ተጠቃሚ ማድረግ ችለዋል፡፡
ሌላዋ የማህበሩ አባል ወይዘሮ ገነት ጌታቸውም ከመደራጀታቸው በፊት ስራ አልነበራቸው፡፡ አሁን ላይ ግን ከተለያዩ ስልጠናዎችና ከጓደኞቻቸው በመማር “የተዋጣልኝ ባለሙያ ሆኛለሁ” ይላሉ፡፡ ስራ የሌላቸውና አንዳንዶቹም በሚሰሩት ልክ ተጠቃሚ የማይሆኑ ሴቶች በየአካባቢው መኖራቸውን የጠቆሙት ወይዘሮዋ ሁሉም ተባብሮ ዘለቄታዊ ተጠቃሚነታቸው እንዲረጋገጥ ሀላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
በባዛርና ኢግዚቢሽን አውደርዕዮች በመሳተፍ ምርቶታቸውን ለተጠቃሚው እያስተዋወቁ የሚገኙት እንስቶቹ እንደነሱ ተደራጅተው አልጋዎችንና ሌሎች የእንጨት ስራዎችን ለሚያመርቱ አንቀሳቃሾች የአልጋ ርብራብ በማቅረብ ተሳስረው እንደሚሰሩ ማረጋገጥ ችለናል፡፡
ሌላኛዋ እንስት ወይዘሮ አልማዝ ሙሉጌታ ይባላሉ፡፡ በተመሳሳይ ከመደራጀታቸው በፊት የቤት እመቤትና “ስራ አጥ” እንደነበሩ ይናገራሉ፡፡ አሁን ላይ ግን እኛም እንዳየናቸው ለወሬም ጊዜ የላቸውም፡፡ ሙሉ ሀሳባቸውንና ትኩረታቸውን በስራቸው ላይ አድርገው የተለያዩ የብረታ ብረት ምርቶችን በደስታ ሲሰሩ ታዝበናል፡፡ አሁን ላይ የስራ ባለቤት በመሆናቸው ኑሯቸውን በተሻለ ሁኔታ እየመሩ እንደሚገኙ ይናገራሉ፡፡
የህብረት ሽርክና ማህበሩ ከአባላቱም ባለፈ ለሁለት ሴቶችና ለአንድ ወንድ የስራ እድል ፈጥሯል፡፡ አጠቃላይ ካፒታሉንም በተደራጁ በአንድ አመት ውስጥ 150 ሺህ ብር አድርሷል፡፡ በዚህም ለሌሎች ዜጎችም የስራ እድል መፍጠር ችሏል፡፡
ወጣት ተመስገን በየነ በማህበሩ ተቀጥሮ መስራት ከጀመረ ስምንት ወር ሆኖታል፡፡ በተመሳሳይ ሙያ ሌላ ቦታ ሲሰራ እንደነበረ ይናገራል፡፡ በክፍያ ደረጃ ያን ያህል ልዩነት ባይኖረውም “የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” ነውና የእንስቶቹ የስራ ጥራትና የወደፊት አላማ እርሱንም ማርኮት አብሮ እንደሚለወጥ በመተማመን ስራውን በአግባቡ እየሰራ ይገኛል፡፡
በቅርቡም ይህንን ስኬታማነታቸውን ያረጋገጠው ሽሮ ሜዳ ቴክኒክና ሙያ ተቋም ከሚያደርግላቸው የስልጠና ድጋፍ በተጨማሪ የቴክኖሎጂ ሽግግርም አድርጎላቸዋል፡፡ ተቋሙ ባሉት አሰልጣኞችና ሰልጣኞች የተሰሩ የተለያዩ ችግር ፈቺ የፈጠራስራዎችን ወደ አንቀሳቃሾች በማሸጋገር እንደነ ሸዋዬና ጓደኞቻቸው የህብረት ሽርክና ማህበር አባላት አይነቶችን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ በቅርቡም ለማህበሩ አባላት የሊስትሮ ባለሙያውንና ጫማውን የሚያስቦርሸውን አካል ምቾት የሚጠብቅና ለከተማው ውበትም የተሻለ ገፅታ የሚፈጥር የሊስትሮ ተንቀሳቃሽ ቤት ሞዴል ሰርቶ እንዳሸጋገረላቸው ወይዘሮ ሸዋዬ ነግረውናል፡፡ በቅርቡም ምርቱን በማምረት ለገበያ እንደሚያቀርቡት ያስረዳሉ፡፡
በመንግስት በኩል ከማደራጀት፣ የመስሪያ ቦታና ብድር እንዲሁም ከገበያ ትስስር ባለፈ ቴክኖሎጂ ስለተሸጋገረላቸው ተደስተዋል፡፡ ከጠበቁት በላይ ድጋፍ እየተደረገላቸው እንደሚገኝ የሚናገሩት እንስቶቹ የገበያ ትስስሩ ግን ተጠናክሮ እንዲቀጥልላቸው ጠይቀዋል፡፡ በተለይም በክፍለ ከተማው በእንጨት ውጤቶች፣ በብሎኬትና በሌሎችም ዘርፎች ተደራጅተው ከሚሰሩ አንቀሳቃሾች ጋር የእርስ በእርስ ትውውቅና ትስስር እንዲፈጥሩ ድጋፍ ቢደረግላቸው የገበያ እጥረቱ እንዳይፈጠር እንደሚያስችል አመላክተዋል፡፡
እኛም የጉለሌ ክፍለ ከተማ ጥቃቅንና አነስተኛ ጽ/ቤት የኢንተርፕራይዞች ልማት ዋና የስራ ሂደት መሪ ከአቶ አብዮት ታደሰ ጋር ባደረግነው ቆይታ በክፍለ ከተማው 2 ሺህ 476 ኢንተርፕራይዞችና 13 ሺህ 133 አንቀሳቃሾች ይገኛሉ፡፡ ከዚህም ውስጥ 4 ሺህ 450 ሴት አንቀሳቃሾች እንደሚገኙ ገልፀው ከወረዳ እስከ ፌዴራል በሚፈጠሩ ባዛርና ኤግዚቢሽኖች ኢንተርፕራይዞች በስፋት እንዲሳተፉና ምርቶቻቸውን ከማስተዋወቁ ባለፈ እርስ በእርሳቸው በመተዋወቅ በዘላቂነት አብረው የሚሰሩበት መንገድ መኖሩንና በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነግረውናል፡፡
እንስቶቹ በቀጣይ ስራቸውን በኢንዱስትሪ ደረጃ የማሳደግ ህልም አላቸው፡፡ በርካታ ሴቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ የማድረገ ውጥንም ይዘዋል፡፡ ለዚህ ስኬታቸውም የህብረተሰቡና የሚመለከተው ባለድርሻ አካል ድጋፍም እንደማይለያቸው እንተማመናለን፡፡

Sunday, 15 May 2016

“ተግባርና ሳይንስ ዓለምን ይለውጣሉ”

ትውልደ ሩሲያዊው ስመጥር ደራሲ ማክሲሞ ጎርኪ “ተግባርና ሳይንስ ዓለምን ይለውጧታል” ሲል መናገሩን ታሪክ መዝግቦታል፡፡ የዚህ ታዋቂ ደራሲ ንግግር የያዘው መልዕክት ጥልቅ ምርምር የሚያስፈልገው አይደለም ቀላልና ግልፅ ነው፡፡ ንግግሩ በተግባር የተደገፈ ሳይንሳዊ ምርምርና፤ የተፈተነ የፈጠራ ውጤት የምንኖርባት ዓለምን እጅጉን ቀላልና ለሰው ልጅ ምቹ በማደረግ የማይተ ሚነና እንዳላቸው የሚያስገነዝብ አባባል ነው፡፡
እንደ አብዛኛው የአለማችን ክፍል አገራችን ኢትዮeያም ከቅርብ አመታት ወዲህ ለሳይንሳዊ ምርምርና ፈጠራ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት አያሌ ተግባራትን በማከናወን ላይ ትገኛለች”” በመሆኑም ከዚህ ቀደም በውስን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ብቻ ታጥሮ የነበረው ምርምርና ፈጠራ ዛሬ እስከ መጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ድረስ መዝለቅ ችሏል”” የእለት ተእለት የመማር ማስተማሩ ሂደትም አንዱና ዋነኛው አካል ከሆነም ሰነባብቷል፡፡ ይህ የምርምር ስራም የትኩረት አቅጣጫውን ችግር ፈቺ በሆኑ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የፈጠራና የምርምር ውጤቶች ላይ አድርጓል፡፡
በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ በኩል ምርምር ለሀገሪቱ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት አገልግሎት ጉልህ አስተዋፅኦ እንዲያበረክት ለማድረግ ዘርፉን ለማበረታታትና የመማር ማስተማሩ ሂደት አብይ አካል በማድረግ በርካታ ስራዎች በመሰራት ላይ ናቸው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ቢሮው ለታለመው የትምህርት ጥራትም ግብ መምታት የምርምር ስራው የማይተካ ሚና እንዳለው በመገንዘብ ወደ ተግባር ገብቷል፡፡
ባለፉት አመታት የትምህርት ሽፋንና ተደራሽነትን በከተማው በሚፈለገው ደረጃ ለማድረስ ቢሮው በርካታ ስራዎችን ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በቢሮው መረጃ መሰረት በከተማው ያለውን የቅድመ መደበኛ ትምህርት ሽፋን እንኳ ብንመለከት 159 የመንግስት የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ ተደርጓል፡፡ የግል ባለሀብቱ በዘርፉ እንዲሳተፍ ምቹ ሁኔታዎችን በመፈጠሩም ከአምስት አመት በፊት 998 ብቻ የነበረው የቅድመ መደበኛ ተቋማት ብዛት በ2007 ዓ.ም 1 ሺህ 92 በመድረስ እድገት አሳይቷል፡፡ ከተቋማቱ መስፋፋት ባልተናነሰ የቅድመ መደበኛ ተማሪዎች ቁጥርም ከነበረበት 118 ሺህ 840 ወደ 157 ሺህ 457 አድጓል፡፡
እድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ዜጎችን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ለማዳረስ አዳዲስ ትምህርት ቤቶችና የማስፋፊያ ግንባታዎችን በማካሄድ ከ5 አመት በፊት 730 ብቻ የነበረው የትምህርት ቤቶች ብዛት 792 ማድረስ ተችሏል”” በአሁኑ ሰአት በከተማችን የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪዎች ቅበላም ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ሆኗል፡፡ 168 ብቻ የነበረው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ብዛትም ወደ 310 ደርሷል”” በዚህም በከተማው የፈረቃ ትምህርት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ወደሙሉቀን ትምህርት ተቀይሯል፤ የክፍል ጥምርታው በአማካይ 45 ደርሷል፡፡ በሁሉም የትምህርት አይነቶች የመፅሀፍ አቅርቦቱ በሁሉም የትምህርት ደረጃዎችና የትምህርት አይነቶች አንድ ለአንድ ደርሷል፤ የመማር ማስተማር ሂደቱን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የማገዙ ስራም ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ ነው፡፡ ባለፉት አመታት የልዩ ፍላጎት ትምህርትም ከፍተኛ ትኩረት ከተሰጣቸውና ፍሬያማ ውጤት ከተመዘገበባቸው የትምህርቱ ዘርፍ አብይት ክንውኖች መካከል አንዱ ነው፡፡ በ2005 ዓ.ም በትምህርት ገበታቸው ላይ 1 ሺህ 922 ብቻ የነበሩትን የልዩ ፍላጎት ተማሪዎች ቁጥር ብዛት ከ6 ሺህ 687 በላይ ማድረስ መቻሉን ከቢሮው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
በከተማችን ከትምህርት ሽፋንና ተደራሽነት ጎን ለጎን የትምህርት ጥራት ማሻሻያ ፓኬጅን በውጤታማነት በመተግበር የትምህርት ውጤት እንዲሻሻል የማድረግ ስራ ተሰርቷል፡፡ ይህን ቁልፍ አላማና ተግባር ከማሳካት አንፃር የትምህርትን ጥራት ለማረጋገጥ እንዲቻል ቢሮው ባዘጋጀው ፓኬጅ ስድስት ዋና ዋና ፕሮግራሞችን ለማካተት እና የአጠቃላይ ትምህርት ስታንዳርድ፣ የሳይንስና ሂሳብ ትምህርትን በግብአት መደገፍ እንዲሁም የ1ኛ ደረጃ ትምህርት ስትራቴጂዎች ተዘጋጅተው ተግባራዊ በመደረጋቸው አበረታች ውጤት ተመዝግቧል፡፡ ትምህርትን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተደራሽ ለማድረግ የሬዲዮ፣ የፕላዝማ፣ የኢንተርኔት ስርጭት በመጀመሩ አይነተኛ ውጤት በመመዝገብ ላይ ነው፡፡ በዚህም በከተማው የብሄራዊ ፈተና ውጤት ላይ የተሻለ ነጥብ የሚያስመዘግቡ ተማሪዎች ቁጥር አሻቅቧል፡፡
ለአብነት በ2007 ዓ.ም በመላው ሀገሪቱ ለ10ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ተቀምጠው 4 ነጥብ ካስመዘገቡ 15 ሺህ 394 ተማሪዎች መካከል 3 ሺህ 958 ያህሉ የአዲስ አበባ ተማሪዎች መሆናቸውን ያገኘነው መረጃ አረጋግጦልናል፡፡
በመጋቢት ወር መጨረሻ ሳምንት በመዲናችን አዲስ አበባ በዳግማዊ ሚኒሊክ የመሰናዶ ትምህርት ቤት ቅጥር ግቢ 6ኛው ከተማ አቀፍ የትምህርት ፌስቲቫልና ኤግዚቢሽን በተለያዩ ፕሮግራሞች ተከብሯል፡፡ በከተማው ከሚገኙ 10ሩም ክፍለ ከተሞች ከሚገኙ የመንግስትና የግል ትምህርት ቤቶች የተወጣጡ መምህራንና ተማሪዎች የተለያዩ ሰራዎችን አቅርበዋል”” በመምህራንና ተማሪዎች የተሰሩ የፈጠራ፤ የምርምር የኪነ ጥበብና የስነ ፅሁፍ ስራዎች ለታዳሚዎች የቀረቡ ሲሆን፤ የጥያቄና መልስ ውድድሮች ተካሂደዋል፤ የግጥምና የስነ ፅሁፍ ስራዎችም ቀርበዋል፡፡ የዚህ የከተማ አቀፍ የትምህርት ፌስቲቫል አንዱ አካል የሆነው ከተማ አቀፍ የትምህርት ምርምር ሲምፖዚየምም ለተከታታይ ሁለት ቀናት በጌትፋም ሆቴል የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሂዶ ነበር፡፡ በመማር ማስተማሩ ሂደት ዙሪያ ባሉ ተግዳሮቶችና መፍትሄዎቻቸው ላይ ትኩረቱን ባደረገው ሲምፖዚየሙ ስምንት ያህል ጥናታዊ ፁሁፎች ቀርበዋል፡፡ በሲምፖዚየሙ የዘርፍ ከፍተኛ ምሁራንን ጨምሮ በከተማና ክፍለ ከተማ የሚገኙ የትምህርት ቢሮ ሃላፊዎች ርዕሰ መምህራን፣ የመንግስትና የግል ትምህርት ቤት መምህራን፣ የወተመህ አደረጃጀቶችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈውበታል፡፡
በሲምፖዚየሙ ከቀረቡ ስምንት ጥናታዊ ፁሁፎች መካከል በቅድመ መደበኛ ትምህርት ላይ ያሉ ተግዳሮቶች፣ የፕላዝማ ትምህርት አጠቃቀም ላይ ያሉ ክፍተቶች፣ ብዝሃነትን መሰረት ያደረገ የትምህርት አሰጣጥን፤ የመምህራንን ሙያዊ ስነ ምግባርን የተመለከቱ ናቸው፡፡ የትምህርት ጥራትን ለማስፈን የመምህራን ሙያዊ ግዴታዎች ምንድናቸው የሚለው ርዕሰ ጉዳይም የውይይት ትኩረት ነበር፡፡ የምርምር ስራዎቹን በሚመለከት ጥናት ያቀረቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና የኮተቤ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ምሁራን ሲሆኑ በተያዘላቸው የጊዜ ቅደም ተከተል መሰረት የጥናታቸውን ግኝት ለተሳታፊዎች አቀርበዋል፡፡ ሲምፖዚየሙ ጥናቶቹን በማቅረብ ላይ ብቻ ያተኮረ ባለመሆኑ ተሳታፊዎች በጥናቶቹ ላይ በተነሱ ክፍተቶችና በተገኙ ግኝቶች ላይ ሰፊ ውይይትና ምክክር አድርገዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲው እጩ የዶክትሬት ዲግሪ አቶ ስመኘው ስንደቄ “Situations of Ecces in addis ababa” በሚል ርዕሰ ጉዳይ በተወሰኑ የመንግስት አፀደ ህፃናት ትምህርት ቤት ላይ ያለውን የቅድመ መደበኛ ትምህርት አሰጣጥ በሚዳስሰው ጥናት ያገኝዋቸውን ውጤቶች አቅርበዋል፡፡
ጥናቱ የመማሪያ ክፍሎችን፣ የመጫወቻ ቦታዎችን፣ የመጫወቻ ግብአት አለመሟላት፣ የመመገቢያ ክፍሎችን አለመኖር፣ የማረፊያ ክፍሎችን ለህፃናቱ እንዲመቹ አድርጎ መስራት ላይ የሚስተዋል ክፍተት መኖሩን አመላክተዋል፡፡ ከዚህ በተነፃፃሪ ውጤታማ የሆነ ሀገራዊ ይዘት ያለው መፅሀፍት በትምህርት ቢሮው በኩል ለአፀደ ህፃናቱ ተማሪዎች ታስቦ መዘጋጀቱን፣ ስራን፣ ጨዋታንና ትምህርትን መሰራት ያደረገው የአፀደ ህፃናት ትምህርት የመማር ማስተማር ዘዴ፣ መስማት ለተሳናቸው ተማሪዎች የምልክት ቋንቋ ክህሎት ያላቸው መምህራንን መመደቡ በትምህርት ቢሮው በኩል በጥንካሬ የሚነሳና የግል አፀደ ህፃናት ትምህርት ቤቶችም ሊማሩበት የሚገባ ጠንካራ ጎን እንደሆነ አመላክቷል፡፡ በሌላ በኩል በዚህ ዘርፍ ከፍተኛ የመምህራን ፍልሰት አለ፤ የሚለው ጥናቱ ይህም መምህራኑ በአፀዳ ህፃናት መምህርነት የቆዩበት ጊዜ እንደስራ ልምድ የማይያዝላቸው መሆኑን በምክንያትነት አንስቷል፡፡
ሌላው በዶ/ር ብርሃኑ አበራ “Some latent problems of plasma based instruction” በሚለው ጥናታዊ ስራቸው ላይ ከፕላዝማ ትምህርት ስርጭት ጋር ተያይዞ በአንዳንድ የመንግስት ትምህርት ቤቶች ላይ ቴክኖሎጂውን በአግባቡ መጠቀም ላይ የሚታዩ ጉድለቶችን አንስቷል፡፡ ትምህርት ቢሮው 400 ሚሊዮን ብር ያህል ከፍተኛ በጀት በመመደብ በአሁኑ ሰአት በአለም ላይ የመጨረሻ የሚባለውን ዘመናዊ የሳተላይት ትምህርት ስርጭት ለዜጎቹ ቢጀምርም አንዳንድ መምህራን ቴክኖሎጂውን በአግባቡ እየተጠቀሙበት እንዳልሆነ ነው በጥናታቸው ያሳዩት፡፡ እንደ ዶ/ር ብርሃኑ ሁሉም ባይባል አንዳንድ መምህራን ይህንየሚያደርጉት ከየእለቱ የትምህርት መርሀ ግብር ጋር በተያያዘ የዝግጅት ማነስና ትኩረት ካለመስጠት ጋር ይመነጫል ነው ያሉት”” በዚህም ምክንያት ተማሪዎች ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅም እያገኙ እንዳልሆነ ነው ያስቀመጡት፡፡ እንደቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ ሃይለስለሴ ፍሠሃ ገለፃ ትምህርት ቢሮው ለወርሃዊ የሳይተላይት (Plasma) ትምህርት ስርጭት ከአንድ ሚሊዮን ብር ያላነሰ ወጪ ያወጣል፡፡ ለአንድ ፕላዝማ ግዥ ብቻ እስከ 15 ሺህ ብር ያወጣል፡፡
የትምህርት ቢሮው በፕላዝማ አጠቃቀም ላይ ለሚታየው ችግር አይነተኛ የሚለውን መፍትሄ አስቀምጧል፡፡ የቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ ሃይለስላሴ ፍሠሃን አነጋግረን በሰጡን ምላሽ ችግሮቹ በመጠኑም ቢሆን አሁን ተፈተዋል ነው የሚሉት”” ቢሮው የትኛው ትምህርት ቤት ቴክኖሎጂውን በአግባቡ እየተጠቀመ ነው? የትኛውን አለአግባብ እየተጠቀመበት ነው? የሚለውን የሚቆጣጠርበት ቴክኖሎጂ ስራ ላይ ማዋሉን ገልፀዋል፡፡ ይህ ዘላቂ መፍትሄ ይሆናል ወይ ስንል ተጨማሪ ጥያቄ አቅርበንላቸው ነበር፡፡ “ይህ ዘላቂ መፍትሄ አይደለም፡፡ ችግሩ ከአመለካከት የመነጨ በመሆኑ አመለካከት ላይ በመስራት ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ርብርብ ማድረግ አለብን” ነው ያሉት፡፡
ሌላኛው በሲፖዚየሙ ከቀረቡ ጥናቶች መካከል “Multi cultural perspectives and challanges in multiethnic school instruction” በሚል ርዕስ በኮተቤ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ የባህልና ቋንቋ መምህርና ተመራማሪ በሆኑት ዶ/ር ፍሠሃ ምቱማ የቀረበው ጥናታዊ ፁሁፍ ነው፡፡ ጥናቱ ትምህርት ቢሮው ብዝሃነትን በአግባቡ የሚያስተናግዱ ዜጎችን ለማፍራት፣ አንዱ የሌላውን ባህል ወግና ቱውፊት የሚያከብር የትምህርት ስርአት መዘረጋቱና፣ በየአመቱ በታላቅ ድምቀት የሚከበሩት የብሄር ብሄረሰቦች ቀን፣ የሰንደቅ አላማ ቀን፣ የትምህርት ሳምንት አውደ ራዕዮች ትልቅ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ያበበባትን ሀገር ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ጥረት በአዎንታዊ መልኩ እየደገፉ መሆናቸውን ጥናቱ አመላክቷል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ የስነ ዜጋና ስነ ምግባር ትምህርትም በህዝቦች ባህልና ወግ እኩልነት ላይ የተመሰረተችውን አዲሲቱ ኢትዮeያ እውን መሆን ላይ ጉልህ አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ምክትል ሃላፊና የትምህርት ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዋና የስራ ሂደት መሪ የሆኑት አቶ ሀይለስላሴ ፍሠሃ የትምህርት ፌስቲቫሉ መከበር በመምህራንና በተማሪዎች ላይ ከፍተኛ የምርምርና የፈጠራ መነሳሳትን እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የትምህርት ፌስቲቫሉ በአጠቃላይ የትምህርት ዘርፍ ላይ ያሉ ችግሮችን ለይቶ ማውጣት ከማስቻሉም በተጨማሪ በቀጣይ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር የጋራ ርብርብ ማድረግ የሚጠይቁ ናቸው ብለዋል፡፡
በሲፖዚየሙ ጥናታዊ ፁሁፋቸውን ካቀረቡ ምሁራን መካከል እጩ የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪ የሆኑት አቶ አወቀ ሸሸጉ አንዱ ናቸው፡፡ ጥሩ የትምህርት ፖሊሲ ስላለ ብቻ የሚፈለገው ውጤት ሊመጣ አይችልም የሚሉት ተመራማሪው መምህራን የተሰጣቸውን ሙያዊ ሃላፊነት በአግባቡ መወጣት እንዳለባቸው ጭምር አስገንዝበዋል፡፡ በየካ ክፍለ ከተማ የመምህራን ማህበር ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ዳኛው አሊ በበኩላቸው በሲምፖዚየሙ የቀረቡ ጥናቶች ከአስተማሪነታቸው ጎን ለጎን ችግሮችን በሚገባ ያሳዩ ናቸው ብለዋል፡፡ በተለይም እንደ የካ ክፍለ ከተማ በቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ላይ ትኩረት ሰጥቶ የተሰራው ጥናትና ምርምሩ ያስቀመጣቸው ክፍተቶች ያሉና በቀጣይ ችግሮቹ ስር ሳይሰዱ ለመፍታት ትልቅ ግብአት እንደሚሆናቸው ተናግረዋል”” በቀጣይም ጥናቱ በዳሰሳቸው ትምህርት ቤቶች ላይ ያሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ከመምህራንና ወላጆች ጋር በጋራ እንሰራለን ነው ያሉት፡፡
በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ከሚገኘው ማርክ ኢንተርናሽናል አካዳሚ የመጡት የትምህርት ቤቱ አካዳሚክ ዲን አቶ ናሆም ፍቅሩ በበኩላቸው በጥናትና ምርምሩ ላይ የቀረቡ ፁሁፎች ያሉብንን ችግሮች በግልፅ ያስቀመጡና ቀላል የሚባሉ ችግሮች በመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ ያላቸውን ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳየ ነበር ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ከተማሪ ወላጆች፤ ከመምህራን ጋር በመሆን እንዴት ችግሮችን በቀጣይ መፍታት እንዳለብን በቂ ግብአት ያገኘንበት ነው ብለዋል፡፡ የትምህርት ሳምንት ፊስቲቫል በከተማ ደረጃ መከበሩ ምርምርና ፈጠራ ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያስመዝገበ ነው ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡን ሌላኛው የሲምፖዚየሙ ተካፋይ አቶ እንዳልካቸው ደጀኔ ከኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው፡፡
ይህ የሰባት መሰረታዊና አንድ መተግባራዊ ጥናት የቀረበበት ሲምፖዚየም ለትምህርቱ ዘርፍ የሚኖረው ጠቀሜታ እጅጉን የጎላ ነው፡፡ ሆኖም ግን ጥናቶቹ የለያቸውን ጠንካራና ደካማ ጎኖች በቅንነት ወስዶ ለመፍትሄው በጋራ መስራት ይጠይቃል”” ያኔ ነው ጥናቱም ግቡን የሚመታው የሚፈለገው ለውጥም የሚመዘገበው፡፡ እነዚህ ችግሮች የሶስቱ የሰራዊት ክንፎች (የህዝብ፤ የመንግስትና የድርጅት) በመገንባትና በማጠናከር ነው መፈታት የሚችሉት የሚል ጠንካራና ግልፅ አቋም በመያዝ ቢሮው በሰራዊት ግንባታ ላይ ይበልጥ ማተኮር ይኖርበታል፡፡
ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ሂደታቸው ሰላማዊነት በቀጣይም የተጠበቀ እንዲሆን፣ በትምህርት ቤቶች የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደርና የኪራይ ሰብሳቢነት ችግሮች ሙሉ በሙሉ እንዲቀረፉ በተለይም ቁልፍ ሚና በሚጫወተው መምህሩ ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት ይገባዋል፡፡
በአብዛኛው በከተማችን ያሉ መምህራን በተግባራቸው ምስጉን ቢሆኑም ጥቂት መምህራን ግን በዚህ መስመር ውስጥ አይደሉም”” መንግስትና ህዝብ ለምስጉን መምህራን ተገቢውን አክብሮት ይሰጣሉ፡፡ ኢኮኖሚያዊ ችግራቸውንም ለመፍታት መንግስትና ህዝብ ሌት ተቀን ይሰራሉ፡፡ ተገቢውን ሃላፊነት በሙያዊ ብቃትና ስነ ምግባር የማይወጡ መምህራን ላይ ፍሬውን ከእንክርዳድ የሚለይ ከሙያ ብቃትና ምዝና ጋር ተያያዥ መሰል ስራዎችን ትምህርት ቢሮው መስራት አለበት፡፡ በጥናቱ የተለዩ ችግሮችን በመፍታትና ጠንካራ ጎኖችን ይበልጥ ፍሬያማ በማድረግ ረገድ የድርጅት ክንፉ (አባል መምህራን፣ የተማሪ አባላት፣ የመሰረታዊ ድርጅት) ሚና ትልቁን ድርሻ ይይዛል፡፡ በመሆኑም በትምህርት ዘርፍ ያለው የድርጅት አባላችን የትምህርት ፓኬጆችን በግንባር ቀደምትነት በማስፈፀም በስራ አፈፃፀሙ የላቀ ሆኖ በመገኘት፣ በስነ ምግባሩም አርአያ በመሆን ሌላውን መምህር በተግባር ተምሳሌትነቱን የመግራት ሃላፊነት አለበት፡፡
በተግባር ሞዴል ሆኖ ከመወጣት ጎን ለጎንም በትምህርት ስርአቱ ውስጥ ሆኖ አፍራሽ ተግባራት የሚፈፅም የተዛባ አመለካከት ያለውን የማስተካከልና የማረም ሃላፊነት እንዳለው አውቆ ሃላፊነቱ በተገቢው መወጣት አለበት፡፡ የትምህርት ጥራት ቁልፍ መሳሪያ ግብአት ሳይሆን የተስተካከለ አመለካከት መሆኑን በመገንዘብ ትምህርት ቢሮም በውጤቶች ብቻ ሳይታጠር ሰራዊት ግንባታም ላይ ዋና ትኩረቱን ማድረግ አለበት፡፡