Saturday, 16 April 2016

የባራክ ኦቦማ ‹‹ኑዛዜ››ና እንድምታዎቹ :ክፍል አንድ { ብሩክ ከድር}



የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ የስልጣን ዘመናቸው መገባዳዱን ተከትሎ ታይምስ ለተባለ ታዋቂ መጽሔት አንድ አነጋጋሪ ቃለ ምልልስ ሰጥተው ነበር፡፡ በቃለ ምልልሳቸው ጎልቶ የወጣው አንድ አነጋጋሪ ነጥብ በስልጣን ዘመናቸው የሰሯቸው ስህተቶችን ዘርዝረው ማስቀመጣቸው ነው፡፡ በተለይ መንግስታቸው ሊቢያን በተመለከተ የተከተከሉትን ፖሊሲ መተቸታቸው ብዙ ነጥቦችን እንድንፈትሽ የሚገፋፋ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ባራክ ኦባማ እንዳሉት "Probably failing to plan for the day after what I think was the right thing to do in intervening in Libya," የሚል ሀሳብ ሰጥተው ነበር፡፡ በሊቢያ ጉዳይ ጣልቃ የገባው መንግስታቸው ከመሃመድ ጋዳፊ መወገድ በኋላ ስለምትመጣው ሀገር ቆም ብሎ አለማሰቡ ስህተት እንደነበር በገሃድ መስክረዋል፡፡
ቁምነገሩ ያለው እዚህ ላይ ነው፡፡ የእሳቸው ንግግር ምን አዲስ ነገር ይዞ መጣ ብለን እናነሳ ይሆናል፡፡ አሜሪካ በየትኛውም ሀገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ገብታ ማን በስልጣን መቆየት እንዳለበት፣ ማን መወገድ እንዳለበት፣ አንዱ ከስልጣን ተወግዶ ቀጣይ ማን እንደሚሆን የመወሰን ስልጣን አላት እንደማለት ነው፡፡ በርግጥ ይህ እውነት አዲስ እውነት አይደለም፡፡ በሊቢያ ጉዳይ አሜሪካና ምዕራባዊያን መንግስታት ጣልቃ ገብተው እንደነበር ለመረዳት ጊዜው አልፏል፡፡  
እ.አ.አ በ2010-2011 በወቅቱ የነበሩት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሂላሪ ክሊንተን በዚህ ረገድ ሚናቸው የጎላ ነበር፡፡ ‹‹የአረቦች ፀደይ›› በመባል የሚታወቀው የአረብ ሀገራት ህዝባዊ መነቃቃት ከወደ ቱኒዚያ መንፈስ ሲጀምር ሊቢያ በአንፃራዊ መረጋጋት ውስጥ ነበረች፡፡ እንዲያውም መሓመድ ጋዳፊ በህዝባዊ ንቅናቄው መጀመሪያ ከስልጣን ለተወገዱት የቱኒዚያ መሪ ቤን አሊ በላኩላቸው የወዳጅነት መልዕክት ‹‹አንተ እኮ ሀገርህን እንደኔ ብትመራት ኖሮ እንዲህ አትሆንም ነበር፣ ድጋፌ አይለይህም›› ብለዋቸው ነበር፡፡ ቆይቶ ግን የተጀመረው ንቅናቄ ወደ ሰሜናዊ የሊቢያ ክፍል ዘልቆ ገባ፡፡ መሐመድ ጋዳፊ ሊቢያ በከፋ አምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ የአንድ ጎልማሳ ሰው ዕድሜን ያህል የመሩ ሰው ናቸው፡፡ በእሳቸው የስልጣን ዘመን ሊቢያዊያን የዴሞክራሲ ሽታ ርቋቸው ስለነበር የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት አይቀሬ ነበር፡፡ ለ42 ዓመታት አምባገነናዊ ስርዓት ያሰፈኑት ጋዳፊ ወንበራቸው መነቃነቁን የተረዱት ምዕራባዊያን መንግስታት በዚህች አጋጣሚ የተነቃነቀውን ወንበር የበለጠ ገፍትሮ ለመጣል በማሰብ ጣልቃ ገቡ፡፡ የተለያዩ ሀገራትን ቅንጅት ፈጥረናል ብለው በዋናነት ግን ትልልቆቹ ምዕራባዊያን ሀገራት የአየር ድብደባ ጭምር አደረጉ፡፡ በሀገር ውስጥ ጋዳፊን ለመጣል መሳሪያ ታጥቀው ከተፋለሙት አማፂያን በላይ በምዕራባዊያን የአየር ጥቃት ብዙ ንፁሃን ህይወታቸውን አጡ፡፡ ጋዳፊም ከተደበቁበት ቱቦ ወጥተው ተገደሉ፡፡
ከዚያ ወዲህ ሊቢያ በሁለት መንግስታት ተከፈለች፡፡ በትሪፖሊ ያለው መንግስትና ቶብሩክ ከተማ ያለው መንግስት ተብለው ሁለት የተለያዩ አስተዳደሮች ‹‹እኔ ነኝ ህጋዊ መንግስት›› ብለው ሀገሪቱን ሰላምና መረጋጋት አሳጧት፡፡ ከዚያም አልፎ ቁጥራቸው እስከ 1700 የሚደርሱ ታጣቂ ቡድኖች ተፈጠሩ፡፡ እነዚህም ባህሪያቸው በአራት ክፍሎች የሚገለፅ ነው፡፡ አንደኛ እስላማዊ ቡድን እንዲፈጠር የሚፈልጉ ታጣቂ ቡድኖች አሉ፡፡ እነዚህ ከለየላቸው ኣሸባሪ ቡድኖች ጋር ግንኙነት ፈጥረው የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ ሁለተኛው እስላማዊ ህገ መንግስት ያለው ነገር ግን ጽንፈኛ ያልሆነ መንግስት እንዲመሰረት የሚፈልጉ አሉ፡፡ ሶስተኛው ምንም ዓይነት ሃይማኖታዊ ገጽታ የሌለውና ሴኩላር መንግስት እንዲመሰረት የሚፈልጉ አሉ፡፡ አራተኛው ደግሞ በውል የሚታወቅ አጀንዳ የሌላቸው ነገር ግን በየአከባቢው ያለውን ነዳጅ ተቆጣጥረው የተወሰነች አከባቢ ብቻ ማስተዳደር የሚፈልጉ የጎበዝ አለቆች አሉ፡፡ ሀገሪቱ እንዲህ ተበታትና መቅረቷ ለፅንፈኛ ቡድኖች ማበብ እድል በመስጠቱ በርካታ ሽብርተኛ ቡድኖች እንዲፈጠሩ አድርጓል፡፡ ከዚህ ውስጥ ዋነኛውና ተጠቃሹ የዓለም ትልቁ አደገኛ አሸባሪ ቡድን (Islamic State) በሊቢያ ውስጥ የራሱ ቅርንጫፍ ከፍቶ እንዲንቀሳቀስ አድርጎታል፡፡ ይህ ቡድን በሰሜን አፍሪካም ሆነ በአውሮፓ ውስጥ ላሉ ሀገራት ከፍተኛ ስጋት የፈጠረ ቡድን ሆኗል፡፡ ሌላው ቢቀር 28 ኢትዮጵያዊያንና ኤርትራዊያንን በሚዴትራኒያን ባህር ወስዶ በግፍ መግደሉ የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው፡፡
ከጋዳፊ መወገድ በኋላ ሊቢያዊያን ጥያቄያቸው ዴሞክራሲ ይምጣልን የሚል መሆኑ ቀርቷል፡፡ አሁን ዋናው ጥያቄ እንደ ሀገር የመኖርና ያለመኖር ሆኗል፡፡ አንድ ሊቢያዊ በሌላ ሀገር ሄዶ ራሱን ሲያስተዋውቅ ‹‹ሀገር አለኝ›› ብሎ በድፍረት የሚናገርበት የዜግነት ፀጋ አጥቷል፡፡ ቢያንስ ሀገሩ ማዕከላዊ መንግስት እንደሌላት ሲያስብ የበታችነት ስሜት እንደሚሰማው ግልጽ ነው፡፡ የአሁኑን የባራክ ኦባማ ‹‹ስህተት ሰርተን ነበር!›› የሚል ንግግር ስናስብ ይህንን ሁሉ እውነታ እንድናነሳ ያስገድደናል፡፡
ከዓመታት ዝምታ በኋላ የመጣው የዚህ ዓይነቱ ‹‹ስህተት ሰርተናል›› ድምዳሜ ምንጩ የምዕራባዊያን መንግስታት የተሳሳተ ፖሊሲ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ባራክ ኦባማ ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት በነበረው የምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ለድል ያበቃቸው አንዱ ነጥብ የጆርጅ ቡሽን የተሳሳተ የውጪ ግንኙነት ፖሊሲ ‹‹አስተካክላለሁ!!›› ማለታቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ በዚህ ረገድ አንዳንድ ‹‹ስኬቶቻቸውን›› መጥቀስ ይቻል ይሆናል፡፡ ነገር ግን አሜሪካና ምዕራባዊያን መንግስታት በአረቡ ዓለም ከተፈጠረው አለመረጋጋት በኋላ እየከፈሉት ያለው ዋጋ ፖሊሲያቸውን እንዲፈትሹ የሚያደርግ ስለመሆኑ ደፍሮ መናገር ይቻላል፡፡ 
የአንድ ሀገር መንግስት ፖሊሲ መመንጨት ያለበት ከህዝቡ ፍላጎት ነው፡፡ አዛዡም መሆን ያለበት የሀገሩ ህዝብ ነው፡፡ አምባገነን መንግስታት በዋናነት ሊዳኙ የሚገባቸው በህዝባቸው ትግልና ከትግሉ በሚመነጭ አጋርነት መሆን አለበት፡፡ ዛሬ በሊቢያ ጉዳይ እንዲህ ዓይነት አቋም ላይ የደረሱት ባራክ ኦባማ በብዙ ሀገራትም ሀገሪቱ የተከተለችው ፖሊሲ ውድቀትን መመስከር አለባቸው፡፡ የዛሬይቱ ዓለም ከቁጥጥርና ‹‹የዓለም ፖሊስነት›› ፍልስፍና ወጥታ የትብብርና አጋርነት (cooperation and partnership) ዓለም ልትቀየር ይገባል፡፡ ምዕራባዊያን መንግስታት ለራሳቸው የሚበጃቸው አሻንጉሊት መንግስት በየሀገሩ ለማስቀመጥ ሲሉ በሚከፍቱት ዘመቻ ደካማ መንግስታት እዚህም እዚያም የሚፈጠሩበት ሁኔታ መቀየር እስካልተቻለ ድረስ ዓለማችን ከተስፋፊነትና አዲስ መልክ ይዞ ከመጣው የኒዮ ሊብራሊዝም  ችግር የምትወጣበት ሁኔታ ሊፈጠር አይችልም፡፡   
የምዕራባዊያን መንግስታት በነዳጅ ላይ ተኮፍሰው ህዝባቸውን ሲበዘብዙ የኖሩትን የአረብ ሀገራት መንግስታት ሲጠብቁና ሲንከባከቡ፣ ገንዘባቸውን በባንኮቹ ሲያከማቹ፣ በመሳሪያ ሀይል ሲደግፉ ቆይቶ የአረብ ሀገራት ዜጎች አምባገነን ሀይሎችን ለማውገዝ ወደ አደባባይ ሲወጡ ‹‹እኛ ከህዝቡ ጎን አለን›› ማለት ጀመሩ፡፡
ታላቁ መሪያችን መለስ ዜናዊ የአረቦች ፀደይ የተሰኘው ህዝባዊ መነቃቃት ከመጀመሩ አስቀድመው በ2000 ዓ.ም በታተመው አዲስ ራዕይ መጽሔት ላይ እንዳስቀመጡት የምዕራቡ ዓለም መንግስታት የአረብ ሀገራትን ወደ ራሳቸው መንገድ በመውሰድ የሃይል ሚዛናቸውን ለማስጠበቅ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፣ ቆመንለታል የሚሉት ሰብዓዊ መብትና ዴሞክራሲ በወረቀት ላይ አስቀርተው ያቀዱትን ለመፈፀም ወደኋላ እንደማይሉ አንስተው ነበር፡፡ ለአብነት አቅርበውት የነበረው የኢራቅ ጉዳይ ብንመለከት ዛሬ ኢራቅ ከነበረችበት አንፃራዊ መረጋጋት ወጥታ የሽብርተኛ ቡድኖች ማዕከል ወደ መሆን የደረሰችው በምዕራባዊያን የተሳሳተ ፖሊሲ መሆኑ ሀቅ ነው፡፡ ከቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት ማብቃት በኋላ ዓለም አንድ አለቃ ብቻ ይዛ ቆይታለች፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ዓለማችን ከአንድ ዋልታ  (Uni Polar) ወደ ብዙ ዋልታዎች (Multi Polar) እየተቀየረች በመሆኑ የበላይነትን አስጠብቆ ለማቆየት በሚደረግ ሩጫ ውስጥ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተረግጠው ተላላኪ መንግስታትን በየአቅጣጫው የመፍጠር ሩጫውን ዓላማችንን ብዙ ዋጋ እያስከፈላት መጥቷል፡፡
ከዚህ ዓለማዊ ሁኔታ ውስጥ የምንወስዳቸው ቁምነገሮች አሉ፡፡ ቀዳሚው ጉዳይ የሀገራት ፖሊሲ መመንጨት ያለበት ከራሱ ብሔራዊ ጥቅም መሆን የሚገባው መሆኑ ነው፡፡ ለዚህም በጽናት የሚቆም ህዝባዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስት መኖሩ ወሳኝ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ ‹‹የኛ መንግስት ቁጭ በል ሲሉት የሚቀመጥ፣ ተነስ ሲሉት የሚነሳ አይደለም፡፡›› ያሉትን እውነታ ደጋግመን ስናስብ ቱኒዚያ፣ ሊቢያ፣ ሶሪያ፣ የመን፣ ኢራቅ፣ ዩክሬን ከዓይነ ህሊናችን ሊጠፉ አይችሉም፡፡     

Wednesday, 13 April 2016

የቴክኖሎጂ ፀጋዎችን አሟጥጦ ያልተጠቀመው የሚዲያ ስራችንና የአዲሱ ሚዲያ አማራጭ ምልከታችን

ብሄራዊ መግባባትና የአስተምህሮ መሳሪያው 
 
 
‹‹ከድህነትና ከኃላቀርነት የመላቀቅ ጥረትና ፍላጎት ስኬታማነቱ የሚወሰነው ጥረቱ በሚመራበት አስተሳሰብ ጥራትና ተቀባይነት ነው፡፡ በአለማችን የተሳካ የልማትና የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ካካሄዱ አገሮችም ሆነ ካልተሳካላቸው አገሮቸ ልምድ በመነሳት ሲታይ በግልፅ የተቀመጠና አብዛኛውን የህብረተሰብ ክፍል አነሳስቶ ለልማትና ለዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ የሚያሰልፍ አስተሳሰብ መኖር አለመኖሩ ከድህነትና ኋላቀርነት የመላቀቅ ፍላጎትን የማሳካት ወይም ያለማሳካት ሚና ይጫወታሉ፡፡›› ይህ እንደ መግቢያ የተንደረደርንበት ሃሳብ በሰላም፣ በዴሞክራሲና በልማት ሃሳቦች ዙሪያ ብሄራዊ መግባባት የመፍጠር አስፈላጊነትና የህዝብ ግንኙነት ስራችን በሚል በ1995 በኋላም የተወሰነ የአርትኦት ስራ ተደርጎበት በ1999 በታተመው መፅሃፍ መግቢያ ላይ የሰፈረ ሃሳብ ነው፡፡
ለእድገትና ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ የሚያበቃ አስተሳሰብ መያዝ አንድ ቁልፍ ጉዳይ ቢሆንም ይህ አስተሳሰብ ስለተያዘ ብቻ ግን ሁሉ ነገር ይሳካል ማለት አይቻልም”” አስተሳሰቡ ቁስ ሃይል ሆኖ ህብረተሰብን መለወጥ የሚችለው አስተሳሰቡን ካፈለቀ ቡድን ወይም ሃይል ወጥቶ ወደ ብዙሃኑ ህዝብ ሲዳረስና የአስተሳሰብ አንድነት ሲፈጠር ብቻ ነው”” ከዚህ አንፃር ትምህርት ቤቶች፣ የመገናኛ ብዙሃን፣ የሀይማኖት ተቋማት፣ የፍትህና የፀጥታ አካላትና ሌሎች የመንግስት አካላት፣የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የህዝብ አደረጃጀቶች ሁሉ የልማትና የዴሞክራሲ አስተሳሰብን ወደ ህብረተሰብ በማስረፅ አይነተኛ መሳሪያዎች ተደርገው ይቆጠራሉ፡፡
በተለይም ከ1993 የድርጅታችን ተሃድሶ በኋላ በበርካታ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ጠንካራ ሃገራዊ መግባባት ተፈጥሯል ማለት ይቻላል፡፡ ከዳር እስከዳር ‹ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው ፈጥነንም መልማት አለብን፤ ይቻላልም› የሚል ሀገራዊ መግባባት ተፈጥሯል፡፡ ከዚህ ጋር ሳይነጣጠልም የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ አስፈላጊነት በመንግስት፣ በድርጅታችን ኢህአዴግና ሌሎች የፖለቲካ ሃይሎች/ከተወሰኑ ፅንፈኛ ሃሎች በቀር/፣ በመንግስትና በህዝብ የማይናወጥ አቋም የተያዘበት አስተሳሰብ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የእነዚህ ሁለት መልካም አስተሳሰቦች ማነቆ ደግሞ በተለያዩ አግባቦች የሚገለፅ ሙስና፣ ጥገኝነት፣ ትምክህት፣ ጠባብነት፣ አክራሪነት፣ አሸባሪነት፣ ተመፅዋችነት... ወዘተ እያልን በመከሰቻ መንገዶች የምንገልፀው እንደ ስርአት ሲጠቃለል የኪራይ ሰብሳቢነት ፖለቲካል ኢኮኖሚ አስተሳሰብ ነው፡፡ ይህንን ፀረ ልማትና ፀረ ዴሞክራሲ አስተሳሰብ ሃገር አጥፊ ነው የሚል ትክክለኛ አስተሳሰብ በመርህ ደረጃ ሙሉ በሙሉ፤ በተግባርም ገዥ በሆነ ደረጃ ብሄራዊ መግባባት የተደረሰበት አጀንዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ስኬቱንም ሆነ ጉድለቱን ህብረተሰቡ በቅጡ እንዲገነዘበው በማድረግ፣ የስኬቱም የጉድለቱም ምንጭ በአግባቡ እንዲገነዘበው በማድረግ ረገድ ደግሞ የተግባር ስምሪቱና አፈፃፀሙ ብቻ ሳይሆን የአስተምህሮትና የህዝብ ግንኙነት ስራችንም ከህዝብ ግንኙነት ስራውም የሚዲያ ዘርፍ የራሱ የማይተካ አስተዋፅኦ ተጫውቷል፡፡ ከዚህ አንፃር የኢንፎርሜሽንና የኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጅ ዘርፍ እድገት ህብረተሰባችን የተሻለ ስፋትና ጥራት ያለው መረጃ እንዲያገኝ እድሎችን አስፍቷል፡፡
እንደሚታወቀው በአለማችን ‹‹አዲስ ሚዲያ›› ወይም ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ›› እንደ አንድ የመረጃ ፍሰት አማራጭ ሆኖ ብቅ ብሏል፡፡ በመሆኑም አዲስ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ ዜጎችና ተቋማት በተለይም በከተሞች ቁጥራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በአለፉት አመታት በ10 ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች የሞባይል ተጠቃሚ መሆናቸውና በኢንተርኔትም በሀገር ደረጃ የ3G ቴክኖሎጂ በተለይም በአዲስ አበባ ደግሞ በዘርፉ የመጨረሻ ትውልድ የሚባለው የ4G ቴክኖሎጂ ስራ ላይ መዋሉ ለመረጃ ልህቀትና ለመረጃ ተደራሽነት ስፋት እድገት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል፡፡ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ምን ያህል የልማትና የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ መሳሪያ መሆን ችሏል፤ የሚለውን ጥያቄ ጥናትም ውይይትም የሚያስፈልገው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡
የሚዲያ እድገት ከጉተንበርግ እስከ ማርክ ዙከርበርግ
የሚዲያ ታሪክ ጀርመናዊ ጉተንበርግ በ1700ዎቹ የህትመት ማሽን ከፈጠረበት ጋር በእጅጉ ይያያዛል፡፡ ከዛን ዘመን ጀምሮ የህትመት ሚዲያና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር እየተመጋገበ ያለንበት እጅግ የላቀ የሚዲያ ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ከህትመት ወደ ሬዲዮ ከሬዲዮ ወደ ተንቀሳቃሽ ምስልና ድምፅን ያወሃደ ቴሊቪዥን እያደገ የመጣው የሚዲያ እድገት እነዚህን አንድ ላይ ነባር ሚዲያ/Traditional Media/ ብሎ በማጠቃለል የኢንተርኔት ቴክኖሎጂን ተከትሎ ራሱን አዲስ ሚዲያ ብሎ የሰየመ አማራጭ ይዞ በ20ኛው ክ/ዘመን ማብቂያ ላይ ብቅ አለ፡፡ ሁሉም የሚዲያ አግባቦች የየራሳቸው ባህሪና ፋይዳ አላቸው፡፡
የዲጂታል ሚዲያ ወይም በተለይም የኢንተርኔት ቴክኖሎጂ በመረጃ ባህሪና ስፋት ስርነቀል ትራንስፎርሜሽን በኮሙኒኬሽን ስርአት ላይ እንደፈጠረ ግን አንድና ሁለት የለውም፡፡ የኢንተርኔት ቴክኖሎጂ እድገትን መከታ አድርጎ ብቅ ያለው አዲስ ሚዲያ ሁሉንም ሰው ጋዜጠኛ አድርጎት አረፈውና ማህበራዊ ሚዲያ የሚል ራሱ በራሱ ካባ ደርቦ የሚዲያ ማህበረሰብን ልብ ማሸፈት ቻለ፡፡
ማህበራዊ ሚዲያ በሌላ አባባል አዲስ ሚዲያ የሚባለው ሲሆን ፈጣን ግንኙነትን በመፍጠር መስተጋብርን በማጠናከር ግንኙነቶችን ውጤታማና ቀላል ማድረግ ችሏል፡፡ ማህበራዊ ሚዲያ ሰዎች በነባሩ ሚዲያ ሲያጋጥማቸው የቆየውን በጊዜና በቦታ የሚወሰን መረጃ የማግኘት እድልን በማስወገድ ያለምንም የጊዜና ቦታ ውስንነት መረጃ እንዲያገኙ አስችሏል፡፡
ዛሬ በእጅዎ የያዙት ሞባይል በየደቂቃ ‹‹አዲስ መረጃ›› አለ እያለ በመደወል ሊያነቃዎና የትም ቦታ ሆነው ራስዎን ከአለም እኩል ሊያራምዱ ይችላሉ በማለት የዘርፉ ሰዎች በግነት ይገልፁታል፡፡
ከዚህም በላይ ነባሩ ሚዲያ ታዳሚያቸውን አንባቢ ወይም አድማጭና ተመልካች በማድረግ ብቻ ወስነውበት የነበረውን ተሳትፎ አዲሱ ሚዲያ ሁሉም ተሳታፊ የመረጃውን ይዘት በማሻሻል ጭምር እንዲሳተፍ አድርጎታል፡፡ ሻይነ ቦውማን እና ቺሪስ ዊሊስ ‹‹ እኛ ሚዲያ›› በማለት እ.ኤ.አ በ2003 ከፃፉት የተሳትፎአዊ ጋዜጠኝነት አስተምህሮ በላይ ልቆ እንዲሄድ አድርጓል፤ አዲሱ ሚዲያ፡፡
“Participatory journalism: The act of a citizen, or group of citizens, playing an active role in the process of collecting, reporting, analyzing and disseminating news and information. The intent of this participation is to provide independent, reliable, accurate, wide-ranging and relevant information that a democracy requires.” We Media:How audiences are shaping the future of news and information,By Shayne Bowman and Chris Willis Edited by J.D. Lasica,2003/
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የአለማችን 42 በመቶ የሚሆነው ህዝብ የኢንተርኔት ተደራሽነት እድል አግኝቷል፡፡ ይህ ማለት ግን ተጠቃሚ ሆኗል ማለት አይደለም፡፡ ይህ በ2014 ከነበረበት 35 በመቶ ሲነፃፀር እድገቱ እጅግ ፈጣን መሆኑን እንመለከታለን፡፡ በ2014 ወደ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን የነበረው የማህበራዊ ሚዲያ ሰራዊት በ2016 መግቢያ ከ3 ቢሊዮን በላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ወቅታዊ መረጃዎች እንደሚነግሩን ገና ከአሁኑ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 3 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ ይህ የኢንተርኔት ቴክኖሎጂ ተደራሽነትም እንደስረአተ ኢኮኖሚው የፍትሃዊ ስርጭት አለመመጣጠን ይታይበታል፡፡ እንደ ባህሬን ያሉት ሃገራት ሙሉ በሙሉ ለህዝባቸው የኢንተርኔት ተደራሽነት ሲያዳርሱ እንደ ሰሜን ኮሪያና ደቡብ ሱዳን ያሉት ደግሞ 0 ነጥብ 1 በመቶ ብቻ መሆኑን መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡ የስርጭት ጉዳይ ሲነሳ በተወሰነ አከባቢ የተከማቸ መሆኑን ልብ ይለዋል፡፡ ስለሆነም አሁንም በበርካታ ሃገራት የነባር ሚዲያ የበላይነት እንደቀጠለ ነው፡፡
ባለንበት አመት 29 በመቶ የአለማችን ህዝብ የዚሁ ማህበራዊ ሚዲያ መደበኛ ተጠቃሚ ሆኗል ተብሎ ይገመታል፡፡ ይህም ማለት ከ2 ቢሊዮን በላይ መደበኛ ተጠቃሚዎቹ አሉ ማለት ነው፡፡ አንድ ቢሊዮን የሚሆኑ ደግሞ በጓደኛቸው ወይም በመስሪያ ቤታቸው ሞባይልና ኢንተርኔት አልያም በኢንተርኔት ካፌ የተለየ ጉዳይ በሚኖራቸው ጊዜ ብቻ አልፎ አልፎ ይጠቀማሉ፡፡
አዲሱ ሚዲያ በፍጥነት እንዲመነደግ እያስቻሉት ካሉት አንዱ መሳሪያ ሞባይል ነው፡፡ ሞባይል በ2016 ከአለም ህዝብ 50 በመቶ እጅ ላይ ይገባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህን እግር በእግር በመከተል ደግሞ የአለም ህዝብ አንድ ሶስተኛ በሶሻል ሚዲያ ይያዛል፡፡ ነባር ሚዲያዎችም ህትመቶቻቸውንና ፕሮዳክሽናቸውን በማህበራዊ ሚዲያው በኩል በተጨማሪ ተደራሽ እያደረጉ ነው፡፡ እንደ ቻይና ደይሊ ያሉት አንጋፋ ጋዜጦች የ3 በአንድ/ ማለትም ጋዜጣን በህትመት፣ በኢንተርኔትና በሞባይል ማሰራጨት/ አደረጃጀት ከፈጠሩ ሰነባብተዋል፡፡
ከአዲሱ ሚዲያ መካከል ትውልድን በማሸፈት ፌስቡክን የሚያህል አልተገኘም፡፡ እጅግ ፈጣን የመረጃ ጎርፍ የሚገማሸርበት ነው”” ከ አንድ ቢሊዮን በላይ ተጠቃሚዎች ያሉት ፌስ ቡክ የዚሁ ገሚሱ የሞባይል ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ በዲጅታል ዘመን ዋናው ተጠቃሚ ወጣት እንደመሆኑም የፌስቡክ ሚዛን የሚወስደው ወጣቱ ነው”” እንደ ሰደድ እሳት ማህበራዊ ሚዲያ ያጥለቀለቃት በተባለችው ናይጀሪያ ወጣቶች ስለሀገራቸውና አለም የተሻለ መረጃ እና ትምህርት እንዲያገኙ አስችሏቸዋል፡፡
እ.ኤ.አ የካቲት 4 2004 የሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ተማሪ በነበረው የ20 አመት ወጣት ማርክ ዙከርበርግ ይፋ የተደረገው የፌስ ቡክ ውልደት ሳይዳኽ የቆመ፤ ወፌ ቆመች ሳይባል የሮጠ የልጆች ጨዋታ የሆነውን የጨቡዴ ዳንዴን ተረት ተረት የሚያስታውሰን ሆኗል፡፡ ሰኞ ተወለደ ማክሰኞ በእግሩ ሄደ እንደተባለው፡፡ በወቅቱ እፍታውን የተጠቀሙት ጥቂት የሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የሆኑ ጓደኞቹ በለጠፈው ፎቶዎች የአመቱ የዩኒቨርስቲውን ቆንጆ ወንድ ተማሪ በመምረጥ ነበር፡፡
እንዲህ እንደዋዛ ብቅ ያለው የወጣቱ ፈጠራ ግን ነባር ሚዲያዎች በ50 አመት ጉዞአቸውም መድረስ ያልቻሉትን በ12 ወራት ብቻ 200 ሚሊዮን ሰዎችን በመረቡ አገናኝቷል፡፡ ሬዲዮ 50 ሚሊዮን ደንበኞችን ለማግኘት ከ35 አመት በላይ፣ ቴሌቪዥን ከ13 አመት በላይ ነበር የፈጀባቸው፡፡
ዛሬ በአጠቃላይ የአዲሱ ሚዲያ ቤተሰብ የሚባለው ከ50 በመቶ በላይ ወይም ወደ 1 ነጥብ 13 ቢሊዮን የአለማችን ሰዎች የፌስቡክ ሰራዊት አባላት ናቸው፡፡ ደንበኞቹ በቀን በአማካይ ከ2 ሰአት እስከ 25 ደቂቃ እንደሚጠቀሙ የፌስ ቡክ ባለቤቶች ይገልፃሉ”” አርጀንቲናውያን እና ፊሊፒኖ ረጂም ሰአት ፌስ ቡክ ተጠቃሚ ተብለው ተፈርጀዋል በቀን እስከ አራት ሰአትና ከዛ በላይ በሶሻል ሚዲያ ይቆያሉ፡፡ 85 በመቶ ደግሞ ፌስ ቡክን በሞባይል ይጠቀማሉ”” እርስዎስ ለምን ያህል ደቂቃ ፌቡክን ይጠቀማሉ?
ቻይናውያን ፌስ ቡክን በሃገራቸው ሙሉ በሙሉ ዘግተውታል”” ፌስ ቡክን በሚተካ በፈጠሩት ማህበራዊ ሚዲያ /Qzone’s/ 629 ሚሊዮን ተጠቃሚዎችን በማፍራት አለምን ይመራሉ፡፡ 1 ቢሊዮን 158 ሚሊዮን 663 ሺህ ህዝብ ያላት አፍሪካ 313 ሚሊዮን 260 ገደማ ህዝቧ ብቻ ነው የኢንተርኔት ተጠቃሚ፡፡ በአህጉሩ በአጠቃላይ በኢንተርኔት ቴክኖሎጂ ተፅእኖ ስር የወደቀ 27 በመቶ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ የራሳቸው አካውንት ያላቸው ግን 9 ነጥብ 6 በመቶ ብቻ ያህሉ ናቸው፡፡
በዚሁ በ2013 በተደረገ ጥናት መሰረት 52 ሚሊዮን አፍሪካውያን በስማቸው የተከፈተ አካውንት ያላቸው ፌስ ቡክ ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ ከ3 ቢሊዮን የኢንተርኔት ተጠቃሚና ከ1 ነጥብ 133 ቢሊዮን የአለም ፌስ ቡክ ማህበረሰብ ጋር ሲነፃፀር የአፍሪካ ድርሻ እጅግ ዝቅተኛ ነው፡፡
ብዙዎች ባለባቸው ቴክኖፎቢያ አዲሱ ሚዲያን ለመቀላቀል፣ ለመቀበልና ለመጠቀም አልቻሉም፡፡ አዲስ ቴክኖሎጂ አለመጠቀም በራሱ ግን አማራጭ አይሆንም የሚለው ሆለሜስ /Holmes.D 2005 communication Theory Media, Technology,society/ እጅግ ጠንካራ ማህበረሰባዊ መስተጋብር ያላቸው ህዝቦች ኢንተርኔትን ጨምሮ አዲስ ቴክኖሎጂን ደፍሮ ያለመጠቀም ፍርሃት እንደሚታይባቸው ይገልፃል፡፡ በሀገራችን ጨምሮ በብዙ ያላደጉ ሀገራት ይህንን አስተሳሰብ ሰፊ ቦታ እንዳለው ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ በእርግጥም የህብረተሰብ የስልጣኔ እድገት ያመጣውን ቴክኖሎጂ መቃወምና አለመጠቀም በራሱ አማራጭ አይሆንም እና ሁላችንም ከዚህ አይነት ፍርሀተ ቴክኖሎጂ መውጣት ይገባናል፡፡
በአፍሪካም ቢሆን የፌስቡክ ባለቤቶች ግን ለውጦችን ማጣጣል የለብንም ይላሉ፡፡ በአፍሪካ /የ2013 መረጃ/ ደቡብ አፍሪካ 7 ነጥብ 3፣ ናይጀሪያ 7 ነጥብ 1፣ ኬንያ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዜጎቻቸው በየቀኑ ማህበራዊ ሚዲያን ይጎበኛሉ፡፡ የአፍሪካን ወጣት ፈጣን መነቃቃት የተገነዘበው ፌስ ቡክ ዋና ትኩረቱን በሶስቱ ሃገራት አድርጓል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በሶስቱ ሀገራት የሚገኙ ዜጎች ለሚዲያው ያላቸው ቅርበትና ተሳትፎ ነው፡፡
የፌስቡክ የአውሮፓ ምክትል ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማንደልሶን የፌስ ቡክ ቀጣይ እድገት ወሳኝ ሚና የምትጫወተው ተጨማሪ ቢሊየን ተጠቃሚዎች የምናመርትባት አፍሪካ ናት ይላል፡፡ስለ አዲሱ ሚዲያ ሲነሳ የተለያዩ አስተሳሰቦች ከተለያየ ማዕዘን ይሰነዘራሉ፡፡ በአንድ በኩል ይህ ሚዲያ ከፋይዳው ይልቅ ጥፋቱ ይበልጣል ከሚል ጀምሮ እጅግ ፅንፈኛ በሆነ ደረጃ ‹‹አጥፊ ነው›› ብሎ ይደመድማል”” ይህንን አቋሙን የሚያጠናክርለት ክስተቶችንም ይጠቃቅሳል፡፡
ሌላኛው ወገን ደግሞ አዲስ ሚዲያ እንደ ማንኛውም ሚዲያ ከሚታይበት ህፀፆች ይበልጥ ፋይዳዎቹ የሚልቅ አለምን በእጅጉ በማስተሳሰር አለም አቀፍ ዜጋ /global citicizen/ መፍጠር የቻለ ነው ብለው በመሞገት በአዲስ ሚዲያ ፈጣን መረጃ ምክንያት ሰዎችን ከእልቂት የታደገባቸውን አጋጣሚዎች ይዘረዝራሉ፡፡ የእነዚህ ሁለት ፅንፈኛ ሞጋቾች መሃል ቦታ የያዙ ወገኖች ደግሞ ነገሩን በሚዛን እንየው፣ በሚዛኑም እንጠቀምበት ይላሉ፡፡
ድማሚት የሰራው ኖብልን በመጥቀስ ሰውየው መቼ ህዝብን የሚጨርስ ፈንጅ ለመስራት አስቦ ፈጠረው ይሉና መልካም ነገር ሁሉ አያያዙ ካልቻሉበት የሚያስከትለው ጉዳት እንዳለ መካድ የለብንም ይላሉ፡፡ እነዚህ ችግሩ ከቴክኖሎጂው ሳይሆን ከአጠቃቀሙ ነው ባይ ናቸው፡፡
እርስዎስ ከየትኛው ወገን ነዎት፣ ማህበራዊ ሚዲያ እንዴትና ለምን አላማ ይጠቀሙበታል? የማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀምዎ ከሃላፊነትዎና ከተሰጠዎት ተልእኮ ጋር የተሳሰረና እንደአንድ የስራዎ አጋዥ ነው የሚጠቀሙበት ወይስ አይደለም? እርስ በራሳችሁ ተወያዩበት አስተያየታችሁንም ፃፉልን፡፡

Sunday, 10 April 2016

አመራሩና ፈፃሚው ለጋራ ዓላማ የተነሱበት መድረክ



ጋቢት 10 በአዲስ አበባ ቲያትርና ባህል አዳራሽ የከተማው የመንግስት ሰራተኛው ለታላቅ ጉዳይ ተሰባስቧል፡፡ አዳራሹ ካፍ እስከ ገደፍ ጢም ብሎ በሰው ተሞልቷል”” ወጣቶች፣ ጉልማሶች፣ መምህራን፣ የጤና ባለሙያዎች፣ የፋይናንስ ባለሙያዎች … የማይታይ የሙያተኛ አይነት የለም፡፡ መቼ ይህ ብቻ የከተማው ከፍተኛ አመራሮችና የቢሮ ሃላፊዎች፣ ክቡር ከንቲባው ጭምር በአዳራሹ ተገኝተዋል፡፡ ምናልባት ይህ አዳራሽ በቅርብ አመታት ውስጥ ይሀን ያህል ብዛት ያለው ሰው አስተናግዶ የሚያውቅ አይመስለኝም፡፡
መቀመጫ ወንበር ያጣው በየደረጃው ላይ ተደራድሯል፡፡ በየግድግዳው ጥግ የቆመውንም ቤቱ ይቁጠረው፡፡ የአዳራሹ ሙቀት ገና ከማለዳው ከፍ ብሏል፡፡ ሙቀቱ ከባህር ጠለል በላይ 2400 ሜትር ከፍታ ላይ የምትገኘው አዲስ አበባ ነው ብሎ መውሰድ እጅጉን ይከብዳል፡፡ ሀቁ ግን ይሄ ነው፡፡ ሙቀቱ ጨምሯል፡፡ ገሚሱ ሙቀቱን ለመከላከል ኮትና ሹራቡን ያወልቃል፡፡ ገሚሱ ማስታወሻ ደብተሩን ያገላብጣል፡፡
በእለቱ የመንግስት ሰራተኛውና አስተዳደሩ ለአንድ አለማ ነበር የተገናኙት፡፡ ይህም ህዝብ ተጠቃሚ የሚሆንበትን ልማትና እድገት ይበልጥ በማረጋገጥና የተጀመረውን የመልካም አስተዳደር ችግር ከስሩ መንግሎ የመጣል ስራ በጋራ እንነሳ የሚልና በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች እየተመዘገበ ያለውን ሁሉን አቀፍ እድገትና የታዩ ክፍተቶችን በተመለከተ በከተማው ውስጥ ካሉ የአስተዳደሩ ሰራተኞች ጋር ለመምከር ነው፡፡ ውይይቱን ያዘጋጀው የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ነው፡፡ ለሁለት ተከታታይ ቀናት የቆየው ይህ ውይይት ከ1200 በላይ ሰራተኞች በ8 የተለያዩ ቡድኖች በመከፋፈል ተሳትፈውበታል፡፡ በቡድን ውይይቶቹ የሞቀ ውይይትና ክርክር ተካሂዷል፡፡
በአብዛኛውም የጋራ መግባባት ላይ በመድረስ ነበር ወደሀይል መድረኩ የቀረቡት፡፡ በሀይል መድረኩ የየቡድኑ ተወካዮች ቡድናቸውን በመወከል አጠቃላይ የቡድን ውይይታቸውን ይዘት አቅርበዋል፡፡ የመኖሪያ ቤት ችግር፤ የኑሮ ውድነት፤ የሰራተኛውና የመምህራን ጥቅማ ጥቅም፤ የትምህርት ጥራት በተመለከተና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ጥያቄዎችም ቀርበዋል፡፡ በተጨማሪም በከተማው የሚታዩ ችግሮች መነሻቸው የመልካም አስተዳደር ችግር ነው፤ አንዳንዶቹም በግልፅ ካለመወያየት የመነጩ ናቸው፤ በመንግስት ሰራተኛው የስራ ዝውውርና የቅጥር ሁኔታ ላይ በፖለቲካ አመለካከትና በብሄረ የሚሰሩ ስራዎች አሉ፤ የመልካም አስተዳደር ችግር ሲፈጥሩ የነበሩ ሰዎች ወደ ካቢኔነት መጥተዋል፤ ከአንድ ቦታ በግምገማ ያነሳችሁትን አመራር ወደ ሌላ የተሻለ ቦታ ትመድባላችሁ የሚሉ ሀሳቦችም ተንፀባርቀዋል፡፡
ከመንግስት ሰራተኛው ለተነሱ የተለያዩ ጥያቄዎች ከመድረክ ምላሻቸውን የሰጡት የፐብሊክ ሰርቪሰና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ሃላፊው አቶ ይስሀቅ ግርማይ ናቸው፡፡ በዘንድሮው አመት ከምን ጊዜውም በተለየ ሁኔታ የከተማችንን የለውጥ ጉዞ ወደ ህብረተሰባዊ የእድገትና ስርነቀል ለውጥ እንቅስቃሴ በማሳደግ ዘላቂ ልማታዊ አስተሳሰብና ተግባር የመገንባት ስራ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው ይላሉ ሃላፊው፤፤፤ዐዐ፡አስተዳደሩ ባለፉት አመታት የመንግስት ሰራተኛውን የትምህርት ደረጃ ለማሻሻል በራሱ ወጪ ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ድረስ ለ658 የመንግስት ሰራተኞች ሙሉ ደሞዝ እየከፈለ ማስተማሩን ለማሳያነት አንስተዋል፡፡

ይህ ተግባር በዘንድሮው አመትም ተጠናክሮ ይቀጥላል የሚሉት ሃላፊው በዘንድሮውም አመት እንዲሁ ከኮተቤ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ 153 ያህል ሰልጣኞች በመጀመሪያ ዲግሪ፣ እንዲሁም 46 የማስተርስ ዲግሪና 2 የዶክትሬት ዲግሪ እጩ ተማሪዎችን በሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ በማስተማር ላይ መሆናቸውን ነው የገለፁት፡፡ ይህ አሀዝ መምሀራን አይጨምርም ያሉት ሃላፊው በክረምት ወደ ትምህርት ገበታ የሚገቡትን መምህራን ቁጥር ሲጨምር በብዙ እጥፍ ከፍ እንደሚል ነው የተናገሩት፡፡
መንግስት የሰራተኛውን የትምህርት ደረጃ ለማሻሻል እያወጣ ያለው ወጪ ከፍተኛ ሀብት ነው ይህንን የመንግስት ሰራተኛው ከግንዛቤ ሊያስገባው ይገባል በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡ መልካም አስተዳደርን ማስፈን ለአመራሩ ብቻ የሚተው ጉዳይ አይደለም፤ ሰራተኛውም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ሲሉ ተጨማሪ ሀሳብ ሰጥተዋል፡፡
በብሄር የስራ ቅጥር ይፈፀማል የሚለው አዲስ አበባን በፍፁም የሚመለከት አይደለም፤ ቢሮው የለየው ዋናው ችግር ዝውውር፣ እድገትና ቅጥር በሚፈፀምበት ጊዜ መመሪያና ደንብን ሳይጠብቁ የሚፈፀሙ ቅጥሮች መኖራቸውን ነው ይላሉ፡፡ በተግባር የተገኙ ችግሮች አሉ ብለዋል፡፡ ለአብነት ባለፉት 10 ወራት ውስጥ ከተፈፀመው 10 ሺህ 97 ያህል ቅጥር ውስጥ ስንፈትሽ 499 የሚሆኑ ከህግና ስርአት ውጪ የተፈፀሙ ቅጥሮችን አግኝተናል፡፡ ቅጥሩ በቀጥታ ውድቅ እንዲሆን ነው ያደረግነው፡፡ ውድቅ ብቻ ማድረግ ሳይሆን ይህን ቅጥር የፈፀመው አካል በህግ ተጠያቂ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ስለዚህ ሲቪል ሰርቪሱ ከአድሎ ነፃ ነው፡፡
የፖለቲካ አመለካከትን መሰረት ያደረገ የቅጥር የዝውውር፤ የደረጃ እድገት ስራ አይሰራም፡፡ መመዘኛችን አጠቃላይ የትምህርት ደረጃና ዝግጁነቱን የአገሪቱን ፖሊሲና እስትራቴጂ የማስፈፀም አቅምን መሰረት ያደረገ አሰራር ነው የምንከተለው፡፡ በመንግስት ሰራተኛችን ውስጥ አባል የሆነ፤ አባል ያልሆነ፤ ገለልተኛ የሆነ ሊኖር ይችላል፡፡ ይህን ሁሉ ያቀፈ ነው የመንግስት ሰራተኛው፡፡ የእኛ የምዘና አሰራር ውጤት ተኮር ነው፡፡ የተሻለ የሰራ የሚሸለምበት፤ ወደኋላ የቀረ የሚደገፍበት ነው፡፡ የፈለገውየፖለቲካ አመለካከት ሊኖረው ይችላል፡፡ ሆኖም ግን አሁንም በተጨባጭ የሚታዩ ችግሮች ካሉ አጣርተን እርምጃ የማንወስድበት ምንም ምክንያት የለም ነው ያሉት፡፡ በምላሻቸው አመራሩም ሆነ ሰራተኛው የህዝብ አገልጋይ ነው ያሉት አቶ ይስሀቅ በመልካም አስተዳደር ጉዳይ ለተፈጠረው ችግር ሁለቱም የድርሻቸውን ይወስዳሉ ብለዋል፡፡
የማጥራት ስራውን በሰፊው ጀምረናል፤ ቁጥራቸው ጥቂት ቢሆንም አሁንም ህዝቡን የሚያንገላቱ ተገቢ አገልግሎት የማይሰጡ እንዳሉ ከህዝቡ ጋር በነበረን መድረክ ለይተናል፡፡ እነዚህም ላይ የማጥራት ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በመሬትና በደንብ ላይ የጀመርነውን ስራ በንግድ፤ በትራንስፖርት በቤቶች ላይም እንዲሁ በንድፈ ሀሳብ ብቻ ሳይሆን በተግባር የማጥራት ስራውን ከዳር እናደርሳለን፡፡ እስከ አሁን የሰራነው ስራ ከህብረተሰቡ ጥያቄ አንፃር በቂ ባይሆንም በጅምር ደረጃ ግን ጥሩ የሚባል ነው፡፡ የህብረተሰቡም አስተያየት በርቱ ከጎናችሁ ነን የሚል ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም በድለላ በኪራይ ሰብሳቢነት ችግር ውስጥ ያለ አመራር በካቢኔነት ተሹሟል ለሚለው አስተያየት ይህ የማይሆን ነው ሲሉ ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡
ምክንያቱም ድለላ ባለቤቱ ሌላ ነው፡፡ አመራር ባለቤት አለው፡፡ አሁንም በተቻለ መጠን አጥርተን በደረስንበት ልክ እርምጃ ወስደናል፡፡ ይህ ሲባል በአመራር፤ በሰራተኛ ላይ ሊሆን ይችላል በተጨባጭ የድለላ ስራ ውስጥ የገባ ካለ በየጊዜው እያጠራን እንሄዳለን፡፡ ስርአታችን እራሱን በራሱ ማጥራት ባህል ስላለው የማናስተካክልበት ምንም ምክንያት የለም”” አስተዳደሩ በምንም ምክንያት ደላላ የሆነ አመራር ካቢኔ የሚያደርግበት ምንም አይነት ፖለቲካዊ ምክንያት የለም፡፡ ሊኖርም አይችልም ነው ያሉት፡፡ በኪራይ ሰብሳቢነት የተገመገመ፤ የስነ ምግባር ችግር ያለበትን ወደኋላፊነት ያመጣንበት ሁኔታ የለም፡፡
በተመሳሳይ ከመኖሪያ ቤት ችግር ጋር ተያይዞ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሻቸውን የሰጡት አቶ ይድነቃቸው ዋለልኝ የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ ናቸው፡፡ ባለፉት 10 አመታት ከ140 ሺህ በላይ በላይ ቤቶች ተገንብተው ለነዋሪዎች ማስተላለፍ መቻሉ ለከተማው አስተዳደር ትልቅ ድል ነው ብለዋል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ የመንግስት ሰራተኛውን የቤት ችግር ለማቃለል ለመንግስት ሰራተኛው ብቻ የ20 በመቶ የልዩ እጣ ተሳታፊ እንዲሆን ወስኖ እየሰራነው ብለዋል፡፡ በዚህ መሰረትም በ2007 ዓ.ም በመጋቢት ወር በወጣው 10ኛው ዙር የቤት ማስተላለፊያ እጣ ብቻ ከተመዘገቡ 18 ሺህ የመንግስት ሰራተኞች ውስጥ ከ10 ሺህ 200 በላይ ሰራተኞች የቤት ባለቤት እንዲሆኑ መደረጉን ተናግረዋል፡፡
በቤት ፈላጊ ምዝገባ ወቅት የተመዘገበው አጠቃላይ ቤት ፈላጊ ከ900 ሺህ በላይ ነው ያሉ ሲሆን ቤቱን ገንብቶ ለማሰረከብ ከ300 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ይጠይቃል ነው ያሉት፡፡ ይህ ወጪ ለህዳሴ ግድብ ከሚያስፈልገው አጠቃላይ ወጪ 3 እጥፍ ማለት ነው ሲሉ የፕሮጀክቱን ግዝፈት ያሳያሉ፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ረጅም ጊዜ፤ ግዙፍ የፋይናንስ አቅም ይጠይቃል ብለዋል፡፡ ሆኖም የከተማው አስተዳደር የቤት ችግሩን ለመቅረፍ ሌት ተቀን እየሰራ ነው ያሉ ሲሆን በአሁኑ ሰአት እንኳ 40 በ60ን ጨምሮ 172 ሺህ ቤቶች በግንባታ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ እስከ አሁንም የከተማ አስተዳደሩ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጎ ግንባታቸውን በማገባደድ ላይ ይገኛል ነው ያሉት፡፡
ከትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ጋር ተያይዞ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሻቸውን የሰጡት የትምህርት ቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ ሀ/ስላሴ ፍሠሀ ናቸው፡፡ የትምህርት ጥራትን በተመለከተ የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣትም የትምህርት ጥራት ፓኬጅን ነድፈን እየሰራ ነው ብለዋል፡፡ የትምህርት ፖሊሲው የሀገሪቷን ቀጣይ የኢንዱስትሪ ሽግግርና የአለምን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ያስገባነው ያሉት ሃላፊው ለትምህርት ጥራትና የወተመህና የመምህራን ሀላፊነትም ጉልህ ድርሻ እንዳለው ገልፀዋል””
ለዚህም የተሻለና ጠንካራ የወተመህ አደረጃጀት ያላቸው ትምህርት ቤቶች የተሻለ ውጤት እያስመዘገቡ ነው ያሉ ሲሆን ወደኋላ የቀሩትም ይህን ተሞክሮ ሊወስዱ ይገባል ነው ያሉት፡፡ የክፍል ጥምርታውን ለማሻሻል ችግሩ በሚታይባቸው የማስፋፊያ አካባቢዎች የትምህርት ቤቶች የማስፋፊያ ህንፃ ግንባታ እየተከናወነ ሲሆን በተሻለ ፍጥነት ላይም ይገኛል ነው ያሉት፡፡
የመምህራንን የእድገት ደረጃ ለማሻሻል በሀገር አቀፍ ደረጃ ምላሽ ለመስጠትም ከሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ቢሮ ጋር በቅንጅት እየሰራን ነው፡፡ በቅርቡም ይፋ እናደርጋለን ነው ያሉት፡፡
አገራችን እያስመዘገበችው ባለው ሁሉን አቀፍ እድገት በከተማችን የነበረው የድህነት ምጣኔ ከነበረበት 29 ነጥብ 6 በመቶ ወደ 18 ነጥብ 9 በመቶ ዝቅ ብሏል ያሉት ደግሞ አቶ ፈይኖ ፎላ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ሃላፊ ናቸው፡፡
እንደአለም ባንክ መረጃ መሰረት የሀገራችን እድገት 11 በመቶ ሆኖ ለረጅም ጊዜያት በዘለቀበትና አለምን ባስደመመበት ወቅት በከተማችን የ14 በመቶ በላይ እድገት መመዝገቡን ነው ያነሱት”” ሆኖም አሁንም አዳጊ የሆነውን የህዝቡን የልማት ጥያቄ በሚገባ ለመመለስ የከተማው አስተዳደር አሁንም የመካከለኛና የረጅም ጊዜ እቅድ አውጥቶ እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
የኑሮ ወድነቱ ከንግድ ስርአቱ መዛባት የመነጨ ነው ለሚለው ጥያቄ ምላሻቸውን የሰጡት የንግድ ቢሮ ሃላፊው አቶ ትዕግስቱ ይርዳውናቸው፡፡ ፍትሃዊ አገልግሎት በመስጠት ዘላቂ ደንበኝነት ያለው አሰራር እንዲኖር ለማድረግ የንግድ ሪፎርም ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል”” ምርቶች ላይ ለጤና ጠንቅ የሆኑ ባዕድ ነገሮችን የመቀላቀልና ሆን ብሎ ሰው ሰራሽ የምርት እጥረት የመፍጠር ዝንባሌዎችን ከህብረተሰቡ በሚቀርቡ ጥቆማዎች መሰረት የማስተካከያ እርምጃ እየወሰድን ነው ብለዋል፡፡
ችግሩን በዘላቂነቱ ለመፍታት የንግዱ ማህበረሰብ ከሸማቾች ማህበረሰብ ጋር ጤናማ ግንኙነት እንዲኖረው ለማስቻል ሰፊ ስራ ይሰራል ነው ያሉት፡፡ ባለፉት 4 አመታት በሸማች ማህበራት አማካኝነት ከአምራች ገበሬዎችና ኢንዱስትሪዎች ጋር በመስራት ሸማቹ ማህበረሰብ የተሻለ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ እያደረግን ነው፤ ሆኖም አሁንም አልፎ አልፎ የሚስተዋሉ እጥረቶችን በተጠና መልኩ ለመቅረፍ በተጠናከረ መልኩ መስራት ይጠበቃል ነው ያሉት፡፡
በውይይቱ ማጠቃለያ ላይ ክቡር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ በተነሱ ጉዳዮች ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ የደሞዝ ጭማሬን በተመለከተ ለተነሳው ሀሳብ የደሞዝ ጭማሪ እንዲሁ በዘፈቀደ የሚደረግ ሳይሆን ኢኮኖሚያችን ባደገ ቁጥር ጥናት ላይ በተመረኮዘ ሁኔታ የሚተገበርነው ብለዋል፡፡ የትራንስፖርት ችግሩን በተመለከተም ለረጅም አመታት የመንግስት ሰራተኛው ችግር ሆኖ የቆየውን የትራንስፖርት ችግር ለመቅረፍ የተወሰደው እርምጃ አስተዳደሩ የመንግስት ሰራተኛውን ችግር ለመቅረፍ ከሰራቸው በርካታ ስራዎች መካከል አንዱ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም የከተማ አስተዳደሩ ከ60 ሺህ በላይ የመንግስት ሰራተኞችን ተጠቃሚ እያደረገ ላለው የፐብሊክ የትራንስፖርት አገልግሎት ከ125 ሚሊዮን ብር በላይ ክፍያ እንደፈፀመ ነው የገለፁት፡፡ በቀጣይም የመምህራንን የስራ መውጫ ሰአት ከግምት ያስገባና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችንም ያማከለ የትራንስፖርት አገልግሎት በከተማው ለመጀመር ቅድመ ሁኔታዎች በመጠናቀቅ ላይ መሆናቸውን ነው የገለፁት፡፡ በዚህም የመንግስት ሰራተኛውን የትራንስፖርት ወጪ ዜሮ ለማድረግ እየሰራን ነው ያሉት፡፡
በተጨማሪም በጋራ መኖሪያ ቤቶች ማሰተላለፍ ላይ ያለው መጓተት ለቤቶቹ የሚያስፈልገውን የመንገድ፤ የውሃና የመብራት የመሰረተ ልማቶችን ሙሉ በሙሉ አሟልቶ ለማስተላለፍ በሚሰራው ስራ አማካይነት ነው የሚፈጠር ነው ብለዋል፡፡ በቀጣይም ይህንን ችግር ለመቅረፍ በተሻለ ፍጥነት በመስራት እልባት ማምጣት እንደሚገባ አስቀምጠዋል፡፡ አያይዘውም በከተማው ካለው የሊዝ ዋጋ አንፃር የቤቶቹ ማስተላለፊያ ዋጋ ከፍተኛ አይደለም ያሉ ሲሆን የከተማ አስተዳደሩ ለቤቶች ግንባታ መሬት በነፃ እያቀረበ ነው ያለው ይህ ደግሞ የነዋሪውን የኑሮ ደረጃና የገቢ መጠን በማገናዘብ የተደረገ ነው ብለዋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ እስከ አሁን በከተማው ይስተዋሉ የነበሩ በርካታ ችግሮችን እየቀረፈ መጥቷል ያሉ ሲሆን ችግሩን መቅረፍ ብቻ መፍትሄ አይሆንም ብለዋል፡፡
ለዚህም ችግር ፈጣሪውን አኳል የማጥራት ስራም የመልካም አስተዳደር ማስፈንና የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግሉ ዋና አቅጣጫ ተደርጎ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ በምላሻቸው መጨረሻ በየትኛውም የመንግስት መስሪያ ቤት የሚገኝ አመራርም ሆነ ፈፃሚ መልካም አገልግሎት የመስጠት ግዴታ አለበት፡፡ ይህንን በአግባቡ ሊወጣ ይገባል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በውይይቱ ላይ የተሳተፈው የመንግስት ሰራተኛው መንግስት በከተማው ከጀመረው ሁሉን አቀፍ የልማትና የመልካም አስተዳደር እንቅስቃሴ ጎን በፅናት እንደሚሰለፍ ድጋፉን አሳይቷል፡፡ በውይይቱ ከተሳተፉ የመንግስት ሰራተኞች መካከል አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ሉሊት መኮንን ከአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ቢሮ የግንባታ ግብአት ቁጥጥር ኬዝ ቲምነው የተገኙት፡፡
የተጀመረውን የመልካም አስተዳደር ስራ ዳር ለማድረስ ይህን የመሰሉ ውይይቶች ጠቀሜታቸው የጎላ ነው ይላሉ፡፡ በውይይቶቹ ላይ በተነሱ ሀሳቦችና ጥያቄዎች ላይ ከመድረኩ የተሰጠው ምላሽ አጥጋቢ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የመልካም አስተዳደር እጦት ቀጥተኛ ተጎጂ የሚሆኑት ሴቶች ናቸው ያሉት አስተያየት ሰጪዋ በፀረ ኪራይ ሰብሳቢነትና መልካም አስተዳደርን የማስፈን ስራ ውስጥም የሚኖራቸው ሚና ጉልህ ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡
ከቂርቆስ ክፍለ ከተማ ዑራኤል 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የመጣው መምህር ስዕሉ ተክሌ በበኩሉ የመምህራንን የትምህርት ደረጃ ለማሻሻል እየተሰሩ ያሉ በጎ ስራዎች ጥሩ ናቸው ያለ ሲሆን ሀገር ሲለማ ሁሉም በየደረጃው ተጠቃሚ ይሆናል፤ መምህራንም የሚጠበቅብንን ሙያዊ ሃላፊነት በመወጣት የተጀመረውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ልንደግፍ ይገባል ብሏል፡፡
በተጨማሪም የትምህርት ጥራትን ማስፈን ለመንግስት ብቻ የሚተው አይደለም ያለ ሲሆን መምህራን በዚህ ረገድ ያለባቸውን ጉልህ ሙያዊ ሃላፊነት በአግባቡ በመወጣት ሊሰሩ ይገባል ነው ያለው፡፡
ከተቀናጀ የመሬት መረጃ ማዕጀከል የተገኙት ወ/ሮ አለምፀሐይ ለማ በበኩላቸው መንግስት አሁን የጀመረውን የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግል በሌሎች ተቋማትም አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባዋል ነው ያሉት፡፡
መልካም አስተዳደርን ማስፈን የህልውና ጉዳይ ነው የሚሉት ወይዘሮዋ ለዚህም የእያንዳንዱ የመንግስት ሰራተኛ ሀላፊነት ከፍተኛ ነው ይላሉ”” በቀጣይ የህዝብ አገልጋይነትን በተግባር በማስመስከር የምንፈልገውን ውጤት ለማስመዝገብ የሞት ሽረት ትግል ልናደርግ ይገባል ብለዋል፡፡
ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ መምህር ሜሮን ጋሹ በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 15 ትምህርት ጽህፈት ቤት የኢኒስፔክሽን ባለሙያ ናት”” የሁለቱ ቀን ውይይት ጥሩ ነበር ትላለች””
በተለይም ለመወያያ የተዘጋጁት ሁለቱም ሰነዶች አጠቃላይ የከተማውን ነባራዊ ሁኔታ የዳሰሱና አሉ የሚባሉ የመልካም አስተዳደር ማነቆዎችን የለየ መሆኑ ይበልጥ አሳታፊ እንዲሆን አድርጎታል ብላለች”” በአጠቃላይ በቡድን ውይይት ወቅት ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከአቅም ግንባታ ቢሮ ሃላፊውና ከክቡር ከንቲባው የተሰጡ ምላሾችም አመርቂና ይበል የሚያሰኙ ናቸው ብላለች””
ለመወያአሁን ላይ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ የህዝብ አጀንዳ ሆኗል”” በተጨባጭ በውይይቱ የታየውም እውነት ይህ ነው፡፡ ለተከታታይ ሁለት ቀናት የተካሄደው ውይይት በአጠቃላይ የህዳሴ ጉዞአችን ዋነኛ ተግዳሮት የሆነውን የመልካም አስተዳደር ችግርና የኪራይ ሰብሳቢነት ፖለቲካል ኢኮኖሚን በማዳከም ልማታዊ ፖለቲካል ኢኮኖሚ የበላይነት እንዲይዝ ጉልህ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡
ይህን መሰል መድረኮች በየጊዜው ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል”” የተሰሩ ስራዎች፤ የተወሰዱ የማጥራት እርምጃዎችን በየጊዜው ለህብረተሰቡ በማሳወቅ የትግል አድማሱን ከዳር ማድረስና የህዳሴያችንን ባቡር በፍጥነት መሳፈር ይጠበቅብናል”” እንላለን”” ሰላም፡፡