Friday, 25 September 2015

የወጣቶች የትግል ጉዞና የቀጣይ ዘመን ተልዕኮ(ለፍትህና እኩልነት የተከፈለ ዋጋ)

ለፍትህና እኩልነት የተከፈለ ዋጋ
የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች በወቅቱ በነበሩት ዴሞክራሲያዊ ድርጅቶች ህወሓትና ኢህዴን/ብአዴን ኋላም ኦህዴድ ውስጥ በመታቀፍ ወጣቱ ሲያነሳቸው ከነበሩት ጥያቄዎች የህዝባዊ መንግስት ምስረታ፣ የእኩል ተጠቃሚነት፣ የብሄርና የኃይማኖት እኩልነት፣ የፍትህና ዴሞክራሲ ጥያቄዎችን ለመመለስ በኢህአዴግ ጥላ ስር ሆነው በፅናት የትጥቅ ትግል አካሂደዋል። በርካታ መስዋዕትነትም ከፍለዋል። ብረት አንስተው በትጥቅ ትግሉ ፍልሚያ የተሳተፉ ታጋዮች ብቻም ሳይሆኑ ንፁሃን የአገራችን ጭቁን ህዝቦች በደርግ የጦር አውሮፕላኖች ዘግናኝ በሆነ መልኩ በጋራ የተፈጁባቸው እንደ ሀውዜን፣ መርሳና በለሳ ያሉ መንደሮች ለፍትህ፣ ለዴሞክራሲና ለብሄር እኩልነት መረጋገጥ ሲባል የተከፈሉ መራር መስዋዕትነቶችን አጉልተው አሳይተዋል። በደርግ የአፈና መዋቅር ከመማረክ ራስን ማጥፋትን የመረጡ ወጣት ታጋዮች በደርጎች እጅ ወድቀው እንኳ ከቆሙለት ዓላማ ፍንክች እንዳላሉ አረጋግጠዋል። እንደ ህወሓት ጓዶች አሞራው (ወልደገሪማ)፣ ቐሺ ገብሩ (ሙሉ ገብረእግዚያብሄር) እንዲሁም እንደ ኢህዴን/ ብአዴን ጓድ ዘለቀ ደምሴ ያሉ በደርግ የግፍ በትር የተገደሉ ታጋይ የኢትዮጵያ ወጣቶች የኢህአዴግ የዓላማ ፅናትና ለህዝቦች ጥቅም ሲባል የተከፈለ መስዋዕትነት የሁልጊዜም ማነፃፀሪያዎች ናቸው። ደርግ ሲያደርሰው ከነበረው ጭፍጨፋ ባሻገር የአገሪቱን ኢኮኖሚ በማዳከም ህዝቡን ለከፋ ድህነት ዳርጓል።

የወጣቶች የትግል ጉዞና የቀጣይ ዘመን ተልዕኮ


በፊውዳሎችና አምባገነኖች ጭቆና ለዘመናት ፍዳቸውን ሲያዩ ከቆዩት የአገራችን ህዝቦች ዋነኛው ገፈት ቀማሽ አርሶ አደሩ ነበር። የከተማ ወጣቶችና ሴቶች የፍትህና የዴሞክራሲ ጥያቄዎችን በማንሳት ለለውጥ ከመሰለፍ ባሻገር አርሶ አደሩ በመሬቱና በምርቱ እኩል ተጠቃሚ ይሁን ብለው በመጠየቃቸው የጭፍጨፋ ሰለባ መሆናቸውም አይዘነጋም፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በማንሳት በተለያዩ ጊዜያት በተደራጀና ባልተደራጀ መልኩ የተካሄዱ ትግሎችም በአርሶ አደሩና አርሶ አደሩን ማዕከል አድርጎ በወጣቶች መሪነት የተካሄዱ ናቸው። ባልተደራጀ መልኩ ጭቆናን ለመናድ በተደረጉ ሙከራዎች የቀዳማይ ወያኔ ትግልና የጎጃምና የባሌ አርሶ አደሮች ያካሄዷቸው አመፆች በቀዳሚነታቸው ይጠቀሳሉ። ምንም እንኳ እነዚህ ያልተደራጁ እንቅስቃሴዎች በወቅቱ ባይሳኩም የወቅቱ ወጣቶች ካለፈው በመማር ጠንካራ የትግል አደረጃጀት እንዲከተሉ መሰረት ሆነዋል፡፡