Monday, 24 August 2015

የኢትዮጵያ ወጣቶችና የመሰረታዊ ለውጥ ትግላቸው part 1

ቅድመ 1983 ዓ.ም የነበረው የፖለቲካ ኢኮኖሚ ሁኔታ በጥቂቱ

ኢትዮጵያ ጥንታዊ አገር ናት፡፡ የአፅመ ቅሪቶችና የሌሎች ማጣቀሻዎች ሳይጨመሩ እስከ አሁን የተደረጉ ጥናቶችንና ስምምነት የተደረሰባቸውን ታሪካዊ ማጣቀሻዎች ብቻ ብንወስድ አገራችንና ህዝቦቿ ከ3 ሺህ ዓመት በላይ ታሪክ ያላቸው ናቸው፡፡ የአገራችን ህዝቦች ጥንታዊ ብቻ ሳይሆኑ ቀድመው ስልጣኔ ከጀመሩ ጥቂት የዓለም አገራት ህዝቦች ተርታ የምንመደብ እንደሆንንም ብዙ የውጭ አገር ምሁራን ሳይቀሩ ያረጋገጡት ጉዳይ ነው፡፡ በምስራቅ አፍሪካ ከእንጨት ቴክኖሎጂ ቀድሞ ከመጀመሩ ጋር ተያይዞ የእርሻ ቴክኖሎጂ በክልላችንም ሆነ በአገራችን ቀድሞ እንደተጀመረ ምርምሮች ያረጋግጣሉ፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ጤፍንና ቡናን ለዓለም ገፀበረከት ማቅረባችን ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ እንስሳትን በማላመድ ጥቅም ላይ ካዋሉ ህዝቦች ተርታም እንደምንመደብ የተረጋገጠ ነው፡፡ በጥቅሉ በግብርናው መስክ ቀድመው ከጀመሩት እንመደባለን፡፡
በግብርና ቴክኖሎጂ ብቻ ሳይወሰን በኪነ-ህንፃ ጥበብም ከግሪክ፣ ከአረቢያና ከአንዳንድ የህንድ አካባቢዎች የሚመጣጠን የዘመናዊ ህንፃ ጥበብን ቀድመን እንደጀመርን አሁን ድረስ ያሉ አሻራዎች ህያው ምስክሮች ናቸው፡፡ የአክሱም፣ የላሊበላ፣ የጎንደር ፣ የሐረር ጀጎል ግንብ፣ በደቡብ የጥያ ትክል ድንጋይ የመሳሰሉት ለዚህ ዋቢ ማሳያዎች ናቸው፡፡ ክልላችንም ሆነ አገራችን ከላይ በተጠቀሱት ሳይወሰኑ የኃይማኖት ብዝሃነትና የቋንቋ ብዝሃነት በሰፈነበት ነባራዊ ሁኔታም ገዥዎቹ እየቆሰቆሱ ከፈጠሩት ግጭት ባሻገር ህዝቦቿ በመግባባትና በመቻቻል ለፍትሀዊ ጥቅም በአብሮነት መኖር ዋና መገለጫቸው ነው፡፡ የራሳችን ፊደል ያለን ከመሆናችንም በላይ በጥበበ ቃላት ግንባታ መነሻ አቅም ነበረን፤ ይህ ደግሞ ለሳይንስና ቴክኖሎጅ እድገት የራሱ አቅም ሊኖረው የሚችል ነበር፡፡ በራሳችን ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ባህል እና እሴት እንዲሁም ሥነ-ልቦና የምንኮራና የውጭ ጠላትን ተደጋጋሚ እና ተከታታይ የጥቃት ሙከራ ተባብሮ በመመከት ነፃነታችንን አስከብረን የመቆየት አኩሪ ታሪክ ያለን ሲሆን የአማራ ክልል ህዝቦችም ለዚሁ አገራዊ ኩራታችን መጠበቅ የበኩላቸውን አኩሪ ተግባር አከናውነዋል፡፡
በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ረገድም አስፋፍተንና አዳብረን አገልግሎት ላይ አላዋልነውም እንጂ የኦሮሞ አባገዳ ስርዓት በየ8 ዓመቱ የስልጣን ሽግግር የሚያደርጉበት ሁኔታ ነበር፡፡ ይህን በምርጫ የሚገለፅ የዴሞከራሲ ገጽታ ያለው የስልጣን ሽግግር በጥናትና ምርምር በማዳበር ለላቀ ጥቅም አውለነው ቢሆን ኖሮ በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታም ቀድመው ከጀመሩት ተርታ መመደብ እንችል ነበር፡፡ ሆኖም በአግባቡ ቀምረን ስራ ላይ ሳናውለው ቆይተናል፡፡
እነዚህ የስልጣኔ አሻራዎች ከ15ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህ አንስቶ እየተሸረሸሩ በመምጣታቸው ድህነትና ኋላቀርነት፣ግጭትና ደም መፋሰስ፣ አለመግባባትና መናቆር እየተከማመሩ ሂደው የማታ ማታ ከ1950ዎቹ እስከ 1980ዎቹ መጀመሪያ እንደ አገር በጋራ የማንቀጥልበት ሁኔታ አንዣብቦ ነበር፡፡ ትልቅ ከነበርንበት ወደ
2
አልተቋረጠ የቁልቁለት ጉዞ ሲያንሸራትቱን የነበሩት ችግሮች ምንድን ናቸው? ብለን ስንመረምር ፊት ለፊት የሚታዩት የብሔሮችና፣ የብሔረሰቦችና የህዝቦች ብዝሃነትንና እኩልነትን የሚያከብር ሁኔታ አለመኖሩ፤ የሃይማኖት እኩልነት አለመከበር፤ የእድገትና ብልፅግና መሰረት የሆኑት መሬት፣ ጉልበት፣ እውቀት እና የካፒታል አቅም በጥቂቶች እጅ ገብቶ ብዙሃኑ የበይ ተመልካች መሆኑ በንድፈ ሃሳብም ሆነ በተግባር ተረጋግጦ ያደረ እውነት ሆነ፡፡
በእኛም አገር ሆነ በሌሎች አገሮች የተደረጉ ጥናቶችና ተግባራዊ ተሞክሮዎች ቀድመው ያደጉ አገሮች የሚያረጋግጡት የእድገታቸው ሚስጥር በህዝባቸው ዘንድ የተሳካ የህግ የበላይነት መረጋገጡ፣ የዜጎች ሀብት የማፍራትና የሀብትና የንብረት ባለቤትነት በአስተማማኝ ሁኔታ መከበሩ፣ የገዥዎች /በስልጣን ላይ ያሉ ስርዓቶች/ ስልጣን የተገደበ መሆን፣ ምንም እንኳ በየአገሩ የነበሩ ኋላቀርና ፀረ-ዴሞክራሲ አገዛዞች ህዝብን ከመበዝበዝና ከመጫን ወደ ኋላ ያሉበት ጊዜ ባይኖርም ቀድመው መለወጥ የቻሉ አገሮች መነሻ ምክንያቱ ስርዓቱ በህግ በተደነገገ የስልጣን ክፍፍል ውስጥ ህዝብ ላይ የሚያሳድረው ጫና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን በህግ የተገደበ መሆኑ፣ ዜጎች አንፃራዊ ነፃነት አግኝተው የግላቸውን፣ የቤተሰቦቻቸውንና የጋራ ልማታቸውን እንዲያፋጥኑና በዚህ ሂደት አማካኝነት የአካባቢና የአገር እድገትም እንዲፋጠን አግዟል፡፡
በእኛ አገር ለዘመናት የቆዩ ስርዓቶች ስልጣናቸው በአግባቡ የተገደበና በታወቀ የህግ አግባብም የሚመሩ አልነበሩም፡፡ እስከ 1970ዎቹ መጨረሻ የነበሩ ስርዓቶች አርሶ አደሮች ያለምንም እገዛ በራሳቸው ጥረት ያመረቱትን ምርት ለገዥዎቹ ይሰፍራሉ፤ የገዛ በሬዎቻቸውንና የእርሻ መሳሪያዎቻቸውን ይዘው ለገዢዎች ያገለግላሉ፤ ደክመውና ጥረው ግረው ያመረቱትን የስርዓቱ ባለስልጣናትን ወታደሮች ይቀሟቸዋል፡፡ በአሰኘው ጊዜ የፈለገውን አይነት መዋጮ ይሰበስባል፡፡
በ1848 ዓ/ም ሰሜን ኢትዮጵያን ለመጎብኘት የመጣና የነበረውን በፍዳና በስቃይ የተሞላውን የአርሶ አደሩን ህይወት በአንክሮ ተመልክቶ የታዘበውን ዋልተር ፕላውደን የተባለ እንግሊዛዊን ጠቅሶ እንደዘገበው «…አርሶ አደሮች ከምርታቸው… ለሹም ይሰፍራሉ፡፡… የገዛ በሬዎቻቸውን ጠምደው የንጉሱንና የአገር ገዥውን መሬት ያርሳሉ። …አባወራው በራሱ ኪሳራ የተወሰኑ ቁጥሮች ያሏቸውን ወታደሮች ይቀልባል። አገር ገዥው በሬ፣ በግ፣ ፍየል፣ ቅቤ፣ ማርና ሌሎች የሚያስፈልጉትን ነገሮች የመውሰድ መብት አለው። ገዥው ከሚገዛቸው አርሶ አደሮች …ባሻው ጊዜ ከእያንዳንዱ አርሶ አደር መዋጮ ይቀበላል።» (የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ... ፤17)
በአማራ ክልልም ሆነ በአገራችን የነበሩ ስርዓቶች የህዝብን ሠላምንና ደህንነትን ጠብቀው በተረጋጋ መልኩ ወደ ልማትና እድገት እንዲረማመዱ የሚያግዙ ሳይሆኑ የላቀ ስልጣን ጨብጠው የአብዛኛዎቹን ህዝቦች ሀብትና ንብረት ለመምጠጥ ሲሉ በሚቆሰቁሱት ጦርነት ህዝቦች ለደህንነታቸው ዋስትና ሳይኖራቸው የኖሩ ናቸው፡፡ ከግብርና ተነስተው ወደ ካፒታል እድገት ለማምራት፣ ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ መስፋፋት ነበረበት፡፡ ህግና ስርዓት በአስተማማኝ ሁኔታ ባልሰፈነበት፣ ለንግድ እንቅስቃሴ የተመቸ የሰውና የሸቀጥ ዝውውር ማድረግ የሚያስችል ሠላማዊ ሁኔታ ባልሰፈነበት ይህን ማከናወን የሚቻል አልነበረም፡፡ በመሆኑም ያደጉ አገሮች ለእድገታቸው ያገዛቸው እነዚህንጉዳዮች ደረጃ በደረጃ እያሻሻሉ መሄዳቸው ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ሁኔታዎች የተመቻቹላቸው ሲሆን በእኛ አገር ደግሞ በተቃራኒው የተመቸ የሠላም፣ የፍትህና የልማት ሁኔታ አልነበረም፡፡
የተጠቀሰው ሁኔታ ዝቅተኛ ምርታማነት ፀንቶ እንዲቆይ ያስገደደ ከመሆኑም በላይ በየወቅቱ እየተፈራረቁ የሚከሰቱ የድርቅ አደጋዎች አርሶ አደሩ ከገዥዎች ምዝበራ ያተረፈውን አንጡራ ሀብት እያደቀቁ ህዝቦቿን ለስቃይና ለሞት ሲዳርጉ ኖረዋል፡፡ የሩቁን ትተን እንኳ ከ1880 እስከ 1980 ለመቶ ዓመት የዘለቀውና ወቅት እየጠበቀ የሚከሰተው ተከታታይ ድርቅና እሱን ተከትሎ የሚስተዋለው ረሃብ በሰውና በእንስሳት ላይ እልቂት የፈጠረበት ሁኔታ እንዳለ ከፊሉን በአይናችን ተመልክተነዋል፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ችግሮች ተደምረው በህዝባችን ውስጥ አልችልም ባይነት፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ተረጅነትና ጠባቂነት ቀላል ባልሆነ ደረጃ ተንሰራፍተው የቆዩበት ሁኔታ ተስተውሎ ቆይቷል፡፡
በአንድ ወቅት ትልቅ የነበርን ቢሆንም ከላይ ዘርዝረን በጠቀስነው ሁኔታ ከትልቅነት ማማ ቁልቁል ተንሸራተን እንደ ህዝብና እንደ አገር በጋራ ያለመኖር አደጋ አናዣቦብን ነበር፡፡ ሆኖም ይህን አስከፊ ሁኔታ ህዝቦች በተናጠልና በጋራ በመሰላቸው አግባብ ታገሉት እንጂ ዝም ብለው አልተመለከቱም፤ አልተቀበሉትም፡፡ በዚሁ ፀረ-ጭቆናና ብዝበዛ ትግል ውስጥ የትላንት ወጣቶች ትግል ግንባር ቀደምና በትውልድ አኩሪ ንቅናቄ ነበር፡፡
1.1.2 የአገራችን ህዝቦች በተለይም የወጣቶች ተጋድሎ
በአገራችን ለዘመናት እየተፈራረቁ የዘለቁ ስርዓቶች ለህዝብ ሠላም፣ ዴሞክራሲ እና በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበትን ስርዓት ለመገንባት ተፈጥሯዊ ሁኔታቸው የማይፈቅድና በመጣጭነት ህዝብን ሲያሰቃዩ የኖሩ በመሆናቸው ህዝቦቹ ከመታገል የቦዘኑበት ሁኔታ እንዳልነበረ ታሪክ ያረጋግጥልናል፡፡ የህዝቦቹ ትግል ያልተደራጀና የተበታተነ ስለነበር በወቅቱ የተደራጀው ፀረ-ዴሞክራሲ ኃይል በቀላሉ ተቆጣጥሮት ዘልቋል፡፡ የሩቁን ትተን ከ1930ዎቹ ጀምሮ እስከ 1980ዎቹ መጀመሪያ ድረስ ጉልህ የሆነ የተደራጀና የተናጠል የህዝቦች ተጋድሎ ተካሂዷል፡፡ በዚህ ውስጥ የወጣቶች ሚና ጉልህ ነበር፡፡
የህዝቡ ተጋድሎ በአጠቃላይ በተለይም ደግሞ የወጣቶች ግንባር ቀደም ንቅናቄ የኢትዮጵያን ንጉሳዊ አገዛዝ ስልጣንን ቀይረው የሚፈልጉትን ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት በወቅቱ መገንባት ባይችሉም ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጋር የተቃኘ የአንገዛም ባይነት ትግል አካሂደዋል። በአማራ ክልል ሁኔታም በ1930ቹ የተካሄደው የጎጃም ገበሬዎች አመጽ፣ በተለያዩ አካባቢዎች የተካሄዱ የአርሶ አደሮችና የየአካባቢው ፊውዳሎች ፍጥጫና የ1964/5 የወሎ ረሃብን ተከትሎ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመጽ ወዘተ… የሚጠቀሱ ናቸው።
የአማራ ክልል ህዝቦችን ጨምሮ የኢትዮጵያ ህዝቦች ፀረ-ብዝበዛና ፀረ-ጭቆና ተጋድሎ ትምህርት ቀመስ በሆነው ኃይል ድጋፍ ማግኘት የጀመረው ከ1950ቹ ወዲህ ነው። በአቤ ጎበኛ እንደተጻፈ ጠቅሶ የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ባሳተመው የአማራ የባህልና ኪነ-ጥበብ መጽሐፍ እንደተጠቀሰው፣
«ተረግጦ ተገፍቶ፤
አልቅሶ ተጠቅቶ፣
ተርቦ ተጠምቶ።
በድንቁርናና በህመም በስቃይ በረሀብ በችግር፣
እየተንገላቱ ዘላለም ከመኖር፣
ከእኩልነትና ከነጻነት ጋር ይሻላል መቃብር።
እንኳን ከውርደት ጋር እንኳን ከችግር ጋር ከደዌ፣ ከጥቃት፣
ከክብርም ጋር ቢሆን ከብዙ ጌትነት፣
ኑሮ ጣዕም የለውም ከሌለው ነጻነት።»
(ባህልና ቱሪዝም ቢሮ; 2001፤ 169)
በዚህ መልክ እየተቀነቀኑ የየህብረተሰብ ክፍሉን የሚያነሳሱ ጽሑፎችና አስተያየቶች መውጣት ጀመሩ። በ1960ቹ ህዝባዊ ትግሉን የተማሪዎች ንቅናቄ የበለጠ ወደ ላቀ ደረጃ አሳደገው። ነባራዊው የህዝቦች መደባዊና ብሔራዊ ጭቆና በድፍረት የተገለጠው ከአማራ ህዝቦች አብራክ በወጣውና የተማሪዎች ንቅናቄ አባልና ግንባር ቀደም መሪ በነበረው የያኔው ዘመን ወጣት ዋለልኝ መኮንን ሲሆን በወቅቱ የሚከተለውን ጽፏል።

Saturday, 22 August 2015

ድልና ድምቀት ለደኢህዴን 9ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ!!

ደኢህዴንና የብሄር ብሄረሰቦች መኖሪያዋ ደቡብ ኢትዮጵያ

ከተመሰረተ 23 አመቱ የሆነው ደኢህዴን እስከአሁን 8 ድርጅታዊ ጉባኤዎችን አከናውኗል፡፡ አሁንም 9ኛ ድርጅታዊ ጉባኤውን ለማከናወን በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ ስለሆነም ጉባኤው ለቀጣይ ለውጥና እድገት ወሳኝ የሆኑ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ጉዳዮች አተኩሮ እንዲሰራ በሚያስችሉ ወሳኝ የሆኑ መነሻ ሁኔታዎች ባሉበት ሁኔታ የሚካሄድ ነው፡፡ በተለይም በ7ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ ‹‹የዕድገትና ትራንሰፎርሜሽን እቅዱን በማሳካት የኢትዮጵያ ህዳሴ ከማይቀለበሰበት ደረጃ እናደርሳለን›› በሚል መሪ ቃል የተካሄደ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእቅዱም በሁሉም መስኮች ተደማሪ ሳይሆን አሸጋጋሪ ውጤት የሚያመጡ ግቦች በተለጠጠ ሁኔታ በማቀድ ነበር ወደ ተግባር የተገባው”” በዚሁ መሰረትም ባለፉት አመታት የክልሉ ኢኮኖሚ በአማካይ በ10 ነጥብ 4 በመቶ አድጓል፡፡
ስለሆነም የክልሉ የምርት መጠን 62 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ደረጃ የደረሰ ሲሆን 49 በመቶ ድርሻ የነበረው ግብርና አሁንም በኢኮኖሚ እድገቱ የአንበሳ ድርሻ እንዳለው እንገነዘባለን፡፡ በድምርም ኢኮኖሚው ባሳየው እድገት የነፍስ ወከፍ ገቢ 700 ዶላር ይደርሳል ተበሎ ይጠበቃል፡፡
ፈጣን ልማቱ መዋቅራዊ ሽግግርን ከመፍጠር ውስንነት ያለው ቢሆንም  እድገቱ የመነጨው አብዛኛው የክልሉ ህዝብ ከተሰማራበት ግብርና ዘርፍ መሆኑን ስንመለከት የእድገቱን ፍትሃዊነትን ያመላክተናል”” በ1997 በክልሉ የድህነት መጠን 39 በመቶ ገደማ የነበረ ሲሆን በ2007 ወደ 22 በመቶ ማሽቆልቆሉ መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ በተለይም ግብርና የራሱን እድገት እያፋጠነ የሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እድገት እንዲያፋጥን የተሰጠውን ተልእኮ በብቃት ተወጥቷል ማለት ይቻላል ይላል ለአባላት ኮንፈረንስ የተዘጋጀ ሰነድ፡፡ የግብርና አማካይ አመታዊ እድገት 8 ነጥብ 7 በመቶ መመዝገቡ የምግብ ሰብሎች ከነበረበት 23 ሚሊዮን ኩንታል ወደ 34 ሚሊዮን የእንሰትና ስራስር ሰብሎች ከ35 ሚሊዮን አመታዊ ምርት ወደ 74 ሚሊዮን ኩንታል ማድረስ መቻሉ የጥረቱን ዋጋ ያሳያል፡፡

የከተማ ልማት

የከተማ ልማት ዋናው ማእከሉ ኢንዱስትሪ የኢንዳስትሪ ቁልፍ ሞተር ደግሞ ጥቃቅንና አነስተኛ በማድረግ በከተሞች የሚታየውን የስራአጥ ቁጥር በመቀነስ በዛው መጠን ድህነትን ለማዳከም ትኩረት ተሰጥቶት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ስለሆነም ባለፉት ሁለት አመታት ብቻ ለ818 ሽህ 262 የስራ እድል በመፍጠር በ5 አመቱ የእድገትና ትራንስፎርመሽን  ከተያዘው እቅድ በላይ ማሳካት ተችሏል፡፡ ይህም ሆኖ በተለይ ለቋሚ የስራ እድል በቀጣይ ትኩረት የሚሻ ሆኖ ይታያል፡፡ በተለይም ደግሞ ለኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን መነሻ የሚሆነው የመካከለኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪ ከማልማት አንፃር ያለው ጉድለት የጉባኤው የውይይት ትኩረት ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

መሰረተ ልማት

መንገድ አንድ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት ወሳኝ ሚና የሚጫወት መሠረተ ልማት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ባለፉ ስርዓቶች ሰፊ የብሄ ብሄረሰቦች  ስብጥር የሚታይበት ክልሉ በአጠቃላይ ልማት እንዲሁም በመሰረተ ልማት የተዘነጋና እርስ በራሱ የቅርብ ሩቅ ሆኖ መቆየቱም ይታወቃል፡፡
 በደኢህዴን መሪነት የክልሉ አስተዳደርና የፌደራል መንግስት ይህንን የቆየ መጥፎ ገፅታ ለመቀየር ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት በክልሉና በፌደራልመንግስት በተከናወነ ስራ 9488 ኪሎ ሜትር አስፋልትና ጠጠር መንገዶች ተገንብቷል”” ከዚህም በተጨማሪ 716 ቀበሌዎችን ከወረዳዎችና ዋና መንገድ ማስተሳሰር ያስቻለ የ2840 ኪሎሜትር መንገድም ተገንብቷል፡፡ ከዚህም ሌላ በክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ለማሻሻል 6364 ተቋማት በመገንባት በጠቅላላ በገጠርና በከተማ 6 ሚሊዮን 557 ሺህ 798  ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል፡፡ በዚህም የክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ ሽፋን 61 በመቶ መድረሱ መረጃዎች ያሳያሉ”” ይህ መረጃ እስከ 2006 የነበረው ብቻ መሆኑ አንባቢው ከግንዛቤ ሊወስድ ይገባል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት በተለይም የሞባይል ተጠቃሚ 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ደርሷል፡፡ 
በድርጅቱ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት መስመር እምነት  መሰረት በእያንዳንዱ ልማት ፍትሃዊ ስርጭቱን መርህ የተከተለ መሆኑን መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ ለምሳሌ ባለፉት አመታት የገጠር ቴሌኮም ፕሮግራም በመዘርጋት 3871 ቀበሌዎች የሽቦ አልባ ስልክ ተጠቃሚ ተደርጓል፡፡ ይህ የቴሌኮም ፕሮግራም ለአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ከሚሰጠው ማህበራዊ አገልግሎት ባለፈ ትልቅ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳም አለው፡፡ ይህም ሆኖ እስከአሁን በመሰረተ ልማት የተሰሩ ስራዎች የክልሉ ህዝብ ለዘመናት የነበረበትን የኢኮኖሚና ማህበራዊ መገለልና ጉዳትን የሰበረ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ድርጅቱና የክልሉ መንግስት ከዚህ በላይ ስራ በቀጣይ እንደሚጠብቃቸው ሳይታለም የተፈታ ነው”” ጉባኤውም በዚህ ዙሪያ ተጨማሪ አቅጣጫዎች ያስተላልፋል ብለን እንጠብቃለን፡፡

ማጠቃለያ

ድርጅታችን ኢህአዴግ ሰኬታማ ድርጅት መሆኑ ብዙዎች የሚመሰክሩት እውነታ ነው፡፡ የድርጅታችን ስኬት በዋነኝነት የሚለካው ድርጅቱ በነደፋቸው እቅዶች በህዝብና በሃገር በመጡት ጥቅምና ፋይዳ ነው፡፡ ከፍ ብለን በወፍ በረር በቃኘነው የክልሎች የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ስኬቶች ከተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እጅግ ጥቂቱን መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል፡፡
በተከታታይ የተመዘገበው ባለሁለት አሃዝ እድገት፣ እንዲሁም ሃገሪቱ በአለም ፈጣን ኢኮኖሚ እያስመዘገቡ ከሚገኙ 10 ሃገሮች አንዷ ሆና ከ10 ዓመታት በላይ መቀጠልዋ፣ እጅግ አለመረጋጋት በሚታይበት የአፍሪካ ቀንድ የሰላም ደሴት የመሆኗ ሚስጢር ፣ በአህጉሪቱ ብቻ ሳይሆን በአለም አቀፍ የተጐናፀፈችው ከበሬታና ተአማኒነት ከድርጅታችን ህዝባዊ መተክሎችና ፕሮግራሞች የመነጩ ናቸው፡፡
ድርጅታችን እስከአሁን ባስመዘገበው ስኬት ደግሞ የሃገራችን ህዝቦች በ5ኛው ሃገራዊ ምርጫ ከመቼውም ጊዜ የላቀ ድምፃቸውን በመስጠት ይሁንታቸውን ሰጥተውታል”” በእነዚህ ድሎች በመታጀብ የሚካሄደው የድርጅታችን ጉባኤ ለቀጣይም የህዝቡን አደራ በላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን ለማሳካት ታሪካዊ ውሳኔዎች እንደሚወስን ይጠበቃል፡፡

Yaa'ii Dhaabatummaa 8ffaa DH. D.U.O yeroo sennaa qabessaa kessatti demsiffammu.ኦህዴድ

Yaa'ii Dhaabatummaa 8ffaa DH. D.U.O Hagayyaa 17-19/2007 yeroo sennaa qabessaa kessatti demsiffammu.
ኦህዴድና የኦሮሚያ ክልል

የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) እስካሁን 7 ስኬታማ ድርጅታዊ ጉባዔዎችን አከናውኗል፡፡ በቅርቡም 8ኛ ድርጅታዊ ጉባዔውን በድምቀት ለማከናወን ዝግጅቱን አጠናቋል!!
ጉባዔው በመጀመሪያው የ5 አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የተጣሉ ክልላዊ ግቦች አፈፃፀማቸውን በመገምገም ስኬታማ አፈፃፀሞች ተጠናክረው የሚቀጥሉበት ጉድለቶችን ፈትሾ የመፍትሔ አቅጣጫ የሚያስቀምጥበት እንደሚሆን ይገመታል፡፡
ኦህዴድ በኦሮሚያ ክልል በሚሰጠው አመራር ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት መመዝገቡ ለኮንፈረንስ የዘጋጀው ሰነድ ያስረዳል፡፡ በገጠርና ግብርና፣ በከተማ ኢንዱስትሪ እንዲሁም በመሠረተ ልማትና ማህበራዊ ልማት በተከናወኑ ስራዎች አማካይ የክልሉ ኢኮኖሚ በ10 ነጥብ 1 በመቶ እያደገ ይገኛል፡፡
በእቅዱና በአቅጣጫው መሠረት ግብርና በአማካይ በ8 ነጥብ 5 በማደግ በኢኮኖሚው የላቀ ድርሻውን እየተጫወተ ይገኛል፡፡ በኢንዱስትሪ በ13 ነጥብ 6 በመቶ እንዲሁም አገልግሎት 10 ነጥብ 7 በመቶ ማደጉንም ሰነዱ አመላክቷል፡፡ በድምር በክልሉ እየተመዘገበ ያለው እድገት ከአጠቃላይ ሀገራዊ እድገት የሚመጣጠን ሆኖ ይታያል፡፡ የተመዘገበው የኢኮኖሚ እድገት በተወሰነም ቢሆን የመዋቅራዊ መተካካት ምልክት መታየቱን ያሣያል፡፡ በ2002 ስንመለከት ከአጠቃላይ ምርት ግብርና የነበረው ድርሻ 59 ነጥብ 2 በመቶ የነበረ ሲሆን በ2007 ወደ 55 በመቶ ዝቅ ማለቱን እንመለከታለን፡፡
በአንፃሩ ከተቀመጠው ግብ አኳያ በቀጣይ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ቢሆንም የኢንዱስትሪ ድርሻ ወደ 11 ነጥብ 2 በመቶ አገልግሎት ከ31 በመቶ ወደ 33 በመቶ ከፍ ብለዋል፡፡ በውጤቱም የክልሉ ህዝብ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ በ2002 ከነበረበት 337 ዶላር ወደ 700 ዶላር ደርሷል፡፡
ኢኮኖሚው የሚያመነጨው ገቢ በአግባቡ በመሰብሰቡ መልሶ ክልላዊ የኢኮኖሚ ግንባታውን በፋይናንስ አቅም ማጠናከር የግድ አስፈላጊ ነበር”” በመሆኑም በመጀመሪያው የትራንስፎርሜሽን የእቅድ ዘመን የክልሉ ገቢ አሰባሰብ እጅግ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደነበር ይታወሣል፡፡ ሰነዱ እንዳመላከተው በ2002 ዓ.ም የተሰበሰበው አመታዊ ገቢ ከ2 ቢሊዮን ብር በታች ነበር፡፡ በዚህ ዘርፍ በተደረገው ሰፊ ርብርብ የገቢ አሰባሰቡ ተሻሽሎ ወደ 10 ነጥብ 89 ቢሊዮን ብር ማድረስ ተችሏል፡፡
ስለሆነም በክልሉ በኢኮኖሚ ልማት በተደረገው ጥረት የዛሬ 10 አመት በክልሉ የነበረው የ37 በመቶ የድህነት መጠን በ2007 ወደ 22 በመቶ ደርሷል፡፡ 

የገጠር ግብርና ልማት

ባለፉት ሁለት አመታት በተቀመረ መልካም ተሞክሮ በተደረገው ጥረት በ2006/7 በተከናወነው የምርት ማስባሰብ ሂደት 133 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ተሰብስቧል፡፡ በ7ኛው መደበኛ ጉበዔ የግብርና ኤክስቴንሽን ወደ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት በ2005 ዓ.ም የነበረው 4 ሺህ 696 የአርሶ አደር እና አርብቶ አደር ማሰልጠኛ ተቋማት በ2007 ዓ.ም ወደ 5 ሺህ 226 አድጓል”” በዚህም የተቋማቱ የሽፋን ስርጭት 81 በመቶ ደርሷል፡፡ በተመሣሣይ አመት የነበረው የአርብቶ አደር እና አርሶ አደር ግብርና ባለሙያ ከነበረበት 19 ሺህ 35 ወደ 20 ሺህ 481 ከፍ በማለቱ በገጠር መንደሮች የሚሰጠው ሙያዊ ድጋፍ ሊጎለብት ችሏል፡፡
በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃም የህብረተሰቡን ተሣትፎ ለማጎልበት በተከናወነው እንቅስቃሴ በህዝብ ተሣትፎ በ2005 ዓ.ም 3 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት መልሶ ማገገም ሲችል፤ በ2007 በድምሩ 5 ነጥብ 6 ሄክታር መሬት ማገገም ችሏል፡፡ በሰው እና እንሰሳት ንክኪ እየተጎዱ ያሉ የመሬት ክፍሎችንም በመከለል የተመዘገበው ውጤት አበረታች ነው፡፡ የቡናን ምርትና ምርታማነትም በ2004/5 ከነበረበት 2 ነጥብ 622 ሚሊዮን ኩንታል በ2006/7 ምርት ዘመን 2 ነጥብ 865 ሚሊዮን ማሣደግ መቻሉ ክልሉ ካስመዘገባቸው ጥቂት የግብርናው ውጤቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

የከተሞችና የኢንዱስትሪ ልማት አፈፃፀም

ሀገራችን ከግብርና መር ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለመሸጋገር የምታደርገውን እንቅስቃሴ ለመደገፍ በሚደረገው ጥረት ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ በከፍተኛ ወጭ የሚገቡ ምርቶችን ለማስቀረት በሀገር ውስጥ ምርቶች የመተካት ተግባር ትኩረት ተሰጥቶታል፡፡
በክልሉ በገጠርና በከተማ የስራ እድል ፈጠራ በተሰጠው ትኩረት መሠረት ከ2 ሚሊዮን 400 ሺህ በላይ ዜጎች የስራ እድል ተፈጥሮላቸዋል”” አፈፃፀሙም ከእቅድ አንፃር 97 ነጥብ 8 በመቶ መሆኑ ተቀምጧል፡፡ ከዚህ ውስጥ የሴቶች ተሣትፎ 33 በመቶ ድርሻን ይዟል፡፡ በቀጣይ ወደ ማኑፋክቸሪንግ የስራ ዘርፍ ለሚገቡ ዜጎች 236 ህንፃዎች በ363 ሚሊዮን ብር ገደማ ተገንብተው ተጠናቀዋል፡፡ ይህም በተለያዩ ከተሞች ለሚነሱ የህዝብ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ናቸው፡፡

መሠረተ ልማት

በአጠቃላይ በ7ኛው ድርጅታዊ ጉባዔ በተላለፈው ሪፖርት መሠረት 24 ሺህ ኪሎ ሜተር የነበረው የመንገድ ርዝመት ባለፉት ሁለት አመታት በተከናወኑ ተግባራት 4 ሺህ 315 የአስፓልት፣ 11 ሺህ 759 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ በፌዴራል እና በክልሉ መንግስት ተገንብቷል፡፡ ስለሆነም በክልሉ 27 ሺህ 534 ኪሎ ሜትር መንገድ በገጠሩ ተገንብቷል፡፡
የንፁህ መጠጥ ውሃ ሽፋንን አስመልክቶ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የተቀመጠውን መቶ በመቶ ለማሣካት በተደረገው ጥረተ ከነበረበት የ60 ነጥብ 6 በመቶ ወደ 88 በመቶ ማሳደግ ተችሏል፡፡

ማህበራዊ ልማት

በትምህርት ዘርፍ የልማት ሰራዊት ከመገንባት አኳያ 15 ሺህ 24 የልማት ሰራዊት፣ 40 ሺህ 539 የ1ለ5 ቡድኖች በማደራች ተልዕኮዎቻቸውን እየተወጡ ይገኛሉ፡፡
በመሆኑም ዴሞከራሲያዊ አመለካከት እና በልማቱ ዙሪያ ያለው የአገልጋይነት መንፈስ መነቃቃት ታይቆበታል፡፡ በኪራይ ሰብሣቢነት አመለካከት እና ተግባር በተደረገው ትግል ይስተዋል የነበረው የትምህርት መንጠባጠብ ወደ 2 ነጥብ 75 ዝቅ ማለት ችሏል፡፡ በተቀናጀ የጎልማሶች ትምህርት በተለያዩ ዙሮች በተሰራው ተግባር ከ2 ሚሊዮን 577 ሺህ 695 ዜጎች ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡
በ2005 መጨረሻ በክልሉ መሠረታዊ የጤና ሽፋን ከነበረበት 90 በመቶ በተያዘው አመት ማገባደጃ ወደ 96 በመቶ ማሣደግ ተችሏል፡፡ ጥራቱን እና ደረጃውን የጠበቀ የጤና አገልግሎት ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ በጤና ተቋማት የውሃ፣ የመበራት፣ መድሐኒት፣ የህክምና ግብአቶች እና የሰለጠነ የሰው ሀይል የተሟላ ለማድረግ ሰፊ ጥረት ተደርጓል፡፡

በዚህ መሠረት የጤና ተቋማትን ተደራሽ በማድረግ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት በ2005 ዓ.ም ከነበረበት 59 በመቶ ወደ 71 በመቶ ከፋ ሲል የወሊድ አገልግሎት ከ17 በመቶ ወደ 74 በመቶ አድጓል፡፡ የድህረ ወሊድ አገልግሎት ሽፋንም ወደ 98 በመቶ አድጓል፡፡ በአጠቃላይ የትምህርት ተደራሽነትን ከማሣደግ፣ ተመጣጣኝ እና ጥራት ያለው የትምህርት ፖሊሲ ተግባራዊ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ በጤና ረገድም የኤክስቴሽን መርሀ ግብር የተቀመጠውን እቅድ ለማሣካት በተደረገው ርብርብ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል፡፡  

ህዝባዊ ሃላፊነታችን ለላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን!!!ድልና ድምቀት ለ11ኛዉ ድርጅታዊ ጉባያችን!!!ብአዴን

ብአዴን እና የአማራ ክልል

የብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ብአዴን/ 11ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ በድርብ ድርብርብ ድሎች ላይ ሆኖ የሚካሄድ ጉባኤ ነው፡፡ በብዙ መለኪያዎች የድል ጉባኤ ነው፡፡ ህዝባዊ ሃላፊነቱን ለላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን ለማዋል በቁርጠኝነት እየተጋ ያለው ብአዴን በ35ኛ አመት የምስረታ በአሉ የሚያካሂደው 11ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ በእርግጥም ልዩ ትርጉም የሚሰጠው ነው፡፡ ብአዴን ከምስረታው እለት አንስቶ በህዝባዊ ወገንተኝነትና በአላማ ፅናት መንፈስ በድል አድራጊነት የዘለቀ አኩሪ ታሪክ ያለው ድርጅት ነው፡፡
ብአዴን በ9ኛውና 10ኛው ድርጅታዊ ጉባኤዎቹ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድን መሰረት ያደረጉ የድርጅትና የመንግስት ስራዎች የሚመራበት አቅጣጫዎች አስቀምጦ ነበር፡፡ በወቅቱ  የድርጅቱ የአቅም ግንባታ ስራ በተለይም የድርጅት አመራሩ ፖለቲካዊና ርእዮተአለማዊ ብቃት ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ነበር ጉባኤው ውሳኔውን አስተላልፎ የነበረ፡፡ በተግባርም አባሉን ጨምሮ በሁሉም የአመራር እርከን የሚገኘው ሃይል በስልጠና የአስተሳሰብ አንድነት ተመጣጣኝነት እንዲኖረው ሰፊ ስራ ተሰርቷል፡፡ በድርጅቱ የሚካሄዱ ኮንፈረንሶች ሳይቆራረጡ ለማካሄድ ከተደረገው ጥረት በላይ ድርጅቱ የተሻለ አቅም የሚፈጥሩ የንድፈ ሃሳብ ትንታኔዎች በማዘጋጀት ለብሄራዊ ድርጅቱ/በተወሰነም ለግንባር አባላት/ በማድረስ የፋናወጊ ሚና ነበረው፡፡

የገጠርና ግብርና ልማት

 በክልሉ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዘመኑ የግብርና ዘርፍ  በ8 በመቶ ለማሳደግ ታቅዶ የነበረ ሲሆን ሙሉ በሙሉ የታቀደው ግብ መድረስ ባይቻልም የተመዘገበው የ7 ነጥብ 2 በመቶ እድገት በምንም መለኪያ ትልቅ የሚባል ነው፡፡ ለምሳሌ የሰብል ምርት የተመለከትን እንደሆነ ወደ 87 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል ከፍ ማለቱን እናያለን፡፡ ከክልሉ አጠቃላይ ምርት ውስጥ ግብርና የ55 ነጥብ 9 በመቶ በመያዝ የክልሉ እድገት ምንጭ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ ክልሉ በምግብ ራሱን ከመቻሉ በላይ ከድህነት ወለል በታች የሚኖረው ህዝብ ከነበረበት 30 ነጥብ 5 በመቶ ወደ 22 በመቶ ዝቅ ማድረግ ተችሏል ተብሎ ይገመታል፡፡ አርሶ አደሩ ምርትና ምርታማነቱን በማሳደግ ከሚደረጉ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች መካከል አርሶ አደሩ በይዞታው ላይ ተማምኖ ዘላቂ ልማት ማምጣት እንዲችል ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚቻል ደረጃ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር እንዲያገኝ ተደርጓል፡፡
የገጠርና የግብርና ልማትና እድገቱ ዘላቂነት የሚኖረው ተፈጥሮን በመጠበቅና የተጎዳውም እንዲያንሰራራ መሆኑ በ10ኛ ጉባኤ ግልፅ አቅጣጫ ያስቀመጠው ጉባኤ በ11ኛው ጉባኤ በስኬት ከሚገመግማቸው ተግባራት አንዱ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ምክንያቱም ከ5 አመት በፊት 7 ነጥብ 9 በመቶ ገደማ የነበረው የክልሉ የደን ሽፋን በዘንድሮ አመት 15 በመቶ መድረስ እንደ ቻለ መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ ይህ ደግሞ በገጠር ጠንካራ የተፈጥሮ ሃብት ሰራዊት መገንባት በመቻሉና የአርሶ አደሩ ጥረት ውጤት ነው ማለት ይቻላል፡፡

የከተማ ልማት

የድርጅቱ ነባር አመራሮች እንደሚገልፁት ድርጅቱ ቆቡን ፈቶ የሚሰፋ ስራ ፈት ድርጅት አይደለም፡፡ የተለያዩ የትምክህትና የጥገኛ ሃይሎች በተደራጀና ባልተደራጀ መልኩ በክልሉ በድርጅቱ እየተገነባ ያለውን ዴሞክራሲያዊ ብሄርተኝነት ግንባታና አስተሳሰብ ለመሸርሸር እንዲሁም በክልሉ የህዝቡን ሁለንተናዊ ኑሮ እየለወጡ ያሉ እድገቶችን ለማጠልሸት ቢፍጨረጨሩም የድርጅቱ አመራርና አባላት ግን ‹‹ እኛ ስራ ላይ ነን›› በማለት ጥርሳቸውን ነክሰው በስራ ላይ ተጠምደዋል፡፡
በክልሉ ከእድገታቸው የገዘፈ ስም የነበራቸው በእድገት ግን የቀጨጩ ከተሞች ከፍተኛ የኢኮኖሚ መነቃቃት ይታይባቸዋል፡፡ የክልሉ ርእሰ ከተማ የሆነችው ባህርዳርን ጨምሮ በርካታ ከተሞች ከስያሜ ባለፈ የእውነተኛ ከተማነት ገፅታ ተላብሰዋል፡፡
በሃገራዊ የከተማ ልማት ስትራቴጂ መሰረት የጥቃቅንና አነስተኛ ልማት የከተማ ልማት እምብርት ነው፡፡ ክልሉም ይህንን አቅጣጫ በመያዝ ስራውን ለማሳካት ያስችላል ያለውን ‹‹የቴክንክና ሙያ ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ›› በማደራጀት በሰራው ስራ በአጠቃላይ 202 ሺህ 274 ኢንተርፕራይዞች የተመሰረቱ ሲሆን በዚሁም በድምሩ ለ2 ሚሊዮን 161 ሺህ 825 ዜጎች የስራ እድል ተፈጥሯል፡፡ በክልሉም 4214 ያህል ሼዶች ተገንብተው ስራ ላይ ውለዋል፡፡ የክልል የካፒታል እቃዎች ና ፋይናንስ አቅራቢ ድርጅትም እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡
በክልሉ የፀና ንግድ ፍቃድ ያላቸው 314 ሺህ 331 ዜጎች ነግደው የሚያተርፉበት እድል ተመቻችቶላቸው እነሱም ከግል ገቢያቸው ባሻገር በክልሉ ልማት እቅድ መሳካት ትልቅ ሚና እያበረከቱ ይገኛሉ፡፡
በአበባና በሰሊጥ የተሰማሩ ኢንቨስተሮችን ጨምሮ በ10 ቢሊዮኖች የሚገመት የኢንቨስትመንት አቅም በክልሉ ተፈጥሯል”” በማኑፋክቸሪንግም ቢሆን በክልሉ 373 አምራቾች ወደ ምርት ተሸጋግሯል፡፡ እንደ ኮምቦልቻ ያሉት የክልሉ ከተሞች ደግሞ ዋናው የሀገሪቱ የኢንዱስትሪ ፓርክ እንዲሆኑ ተለይተዋል፡፡ ሆኖም በክልሉ ካለው እምቅ ሃብት አንፃር የማኑፋክቸሪንግ ንኡስ ዘርፍ ድርሻ መድረስ የነበረበት ደረጃ ደርሷል የሚባል አይደለም፡፡ በባለሃብቱ ዘንድ ወደ አገልግሎት ዘርፉ የማዘንበል ሁኔታዎች እንዳሉ የኢንቨስትመንት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ስለሆነም በቀጣዩ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን በዚህ ረገድ ያለውን ውስንነት በማስወገድ በክልሉ የኢኮኖሚ መዋቅር ሽግግር እንዲሳለጥ የሚያስችል አቅጣጫ ከጉባኤው ይጠበቃል፡፡

መሠረተ ልማት

ዞንን ከዞን፣ ወረዳን ከወረዳ፣ ቀበሌን ከቀበሌ ማዕከል ጋር የሚያገናኙ  መንገዶችና ድልድዮችን በመገንባት እንዲሁም ነባር የገጠር መንገዶችን በመጠገን ያልተቋረጠ አገልግሎት መስጠት እንዲቻል ማድረግ በሚሉ የጉባኤው አቅጣጫ መሰረት ከ9ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ ወዲህ በሁለት አመት ውስጥ 11 ሺህ ኪሎሜትር መንገድ ተገንብቷል፡፡ በእቅድ ዘመኑ 1274 የቀበሌ ማዕከላት ከዋና መንገድ የተገናኙ ሲሆኑ ቀደም ባሉ አመታት ከዋና መንገድ የተገናኙ 725 ቀበሌዎችን ጨምሮ በድምሩ 1999 ቀበሌዎች ከዋና መንገድ ጋር ተገናኝተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ የክልሉ የውሃ ሽፋን በአማካይ 89 ነጥብ 5 በመቶ የደረሰ ሲሆን በድምር 1177 ቀበሌዎች ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ ይህም ሆኖ የኤሌክትሪክ ሽፋኑ እና የሽቦ አልባ ስልኮች ስርጭት በቀጣይ ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ መሆኑንና ጉባኤውም በዚህ ዙሪያ ትኩረት ሰጥቶ ይወያይበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ማህበራዊ ልማት

በክልሉ በትምህርት ዘርፍ የምእተ አመቱ ግብ ለማሳካትና ፍትሃዊነትን ለማረጋገጥ ስኬታማ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡ በእቅድ ዘመኑ በተለይም የቅድመ መደበኛ ትምህርት ተደራሽነትና ተሳትፎ በ2002 ከነበረበት እጅግ ዝቅተኛ የሚባለው የ2 ነጥብ1 በመቶ ወደ 51 ነጥበ 6 በመቶ መድረሱ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ሽፋን ንጥር ተሳትፎ 92 በመቶ፣ የ2ኛ ደረጃ ደግሞ 36 በመቶ የደረሰ ሲሆን  ማንበብና መፃፍ የማይችሉ ጎልማሶች በክልሉ 60 ነጥብ 8  በመቶ የነበረ ሲሆን በተሰራው ስኬታማ ስራ 27 በመቶ የሚሆኑ የጎልማሳ ትምህርት መርሃ ግብር ተምረው ያጠናቀቁ ሲሆን 45 በመቶ ደግሞ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡
ከትምህርት መሠረተ ግንባታ አንፃር 261 ሁለተኛ ደረጃ ተምህርት ቤቶች  እንዲገነቡ ተደርጓል፡፡ የአንደኛ ደረጃ የተማሪ መጠነ ማቋረጥ ወደ 1 ነጥብ 57 በመቶ ዝቅ እንዲል ተደርጓል፡፡ በአንደኛ ደረጃው የወንድና ሴት ተማሪ ተሳትፎ ተመጣጣኝ ደረጃ የደረሰ ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ የሴት ቁጥር ብልጫ እንዳለው መረጃው ያሳያል፡፡
መከላከልን ማዕከል ባደረግው የጤና ፖሊሲ መሰረት የጤና ኤክስተንሽን ፕሮግራም በሁሉም የገጠርና ከተማ ቀበሌዎች ተግባራዊ ሆኗል፡፡ በመሆኑም በክልሉ 89 በመቶ አባወራ/ እማወራ/ በጤና አክስቴንሽን ፓኬጅ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡
በ2002 ከ100 ሺህ እናቶች 676 ይሞትበት የነበረው እውነታ በመቀየር ዛሬ ወደ 420 ዝቅ ብሏል”” የህፃናት ሞትም በሁለት ሶስተኛ መቀነስ ተችሏል፡፡ በክልሉ በርካታ ወረዳዎችና በሺህ የሚቆጠሩ ቀበሌዎች ለአስከፊ የወባ ወረርሽኝ በሽታ ተጋላጭና በሽታው በክልሉ አንደኛ ገዳይ እንደነበረ ይታወቃል”” ነገርግን በዚህ ዙሪያ በተሰራው ስኬታማ ስራ ችግሩ ሙሉ በሙሉ ባይወገድም  ከፍተኛ የጤና ችግር ወደ ማይሆንበት ደረጃ ደርሷል፡፡ ከመከላከል በተጓዳኝ የጤና አገልግሎት ተደራሽነት ማስፋትም ትኩረት የተሰጠው ነበር፡፡ በመሆኑም በክልሉ 820 የጤና ጣቢያዎች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ የሆስፒታሎች ቁጥርም በእቅድ ዘመኑ ከነበረበት 16 ተቋማት  በመገንባት ያሉትን ጨምሮ ወደ 74 ማድረስ ተችሏል፡፡


ዓወትን ድምቀትን ን መበል 12 ውድባዊ ጉባኤ ህወሓት!!

ዓወትን ድምቀትን ን መበል 12 ውድባዊ ጉባኤ ህወሓት!!
ከጉባኤ እስከ ጉባኤ፤  በጨረፍታ (ህዳሴ ጋዜጣ)
ኢህአዴግና የግንባሩ አባል ድርጅቶች ህወሓት፣ ብአዴን፣ ኦህዴድና ደኢህዴን በህገ ደንባቸው መሰረት በየሁለት አመት ወይም በየሁለት አመት ተኩል ድርጅታዊ ጉባኤያቸውን ያካሂዳሉ፡፡ ይህ የድርጅቶቹ ጉባኤ አንዱ የዴሞክራሲያዊ ባህሪያቸው መገለጫ  ነው፡፡ ሌላው የጉባኤ ሂደት ብቁ ቅድመ ዝግጅትና መላው አባላቱን ባሳተፈ መልኩ የግልፀኝነትና አሳታፊነት መርህ ጠብቆ የሚካሄድ መሆኑ ነው፡፡ በሁሉም ድርጅቶች የጉባኤ አዘጋጅ ኮሚቴ የሚደራጅ ሲሆን የጉባኤ የትኩረት አቅጣጫዎች በመለየትና ሰነድ በማዘጋጀት ሁሉም አባላት በሰነዱ ተወያይተው በሚሰጡት ግብአት ቀድመው እንዲያዳብሩት ይደረጋል”” በዚህ ሂደትም በዴሞክራሲያዊ መንገድ በድርጅታዊ ጉባኤ የሚሳተፉ ጉባኤተኞች በአባላቱ ተመርጠው ይላካሉ፡፡
ጉባኤ ወይም ኮንፈረንስ በተለያዩ ስርአቶችና አደረጃጀቶች የሚካሄድ የተለመደ ጉዳይ ነው፡፡ ከሙያ ማህበራት ጀምሮ እስከ ፖለቲካ ድርጅቶች ጉባኤ ያካሂዳሉ፡፡ ነገር ግን ጉባኤዎች እንደየአደረጃጀቶቹ ባህሪና አላማ የተለያየ ፋይዳና ትርጉም አላቸው፡፡ አንዳንድ ጉባኤዎች ለፎርማሊቲ ብቻ የሚካሄዱ፣ ጉዳዮቹ በጉባኤተኛ ሳይሆን በጥቂት የአደረጃጀቱ/ መንግስት፣ ማህበር፣ የፖለቲካ ፓርቲ ወዘተ . . ./ ልሂቃን የሚልቁበትና የሚወሰኑበት ነው፡፡ የኢህአዴግና አባል ድርጅቶች ጉባኤዎች ግን ከፍተኛ ሃገራዊ ፋይዳ ያላቸው ድርጅታዊና ሃገራዊ ጉዳዮች የሚመከሩበትና እቅዶች የሚታቀዱበት ነው፡፡
የየብሄራዊ ድርጅቶች እንደተጠበቀ ሆኖ የኢህአዴግ ጉባኤ ስንመለከት በ1983 በወረሃ ጥር በተንቤን ማይሎሚን ከተካሄደው አንደኛው ድርጅታዊ ጉባኤ ጀምሮ እስከ ባህርዳሩ ዘጠነኛው ድርጅታዊ ጉባኤ የተላለፉ ውሳኔዎች ድርጅቱን ከአንድ ምዕራፍ ወደ ሌላ ምዕራፍ ያሸጋገሩ የየራሳቸው ሃገራዊ አሻራ የነበራቸው መሆናቸውን እንታዘባለን”” ዘንድሮም አራቱም ብሄራዊ ድርጅቶቻችንና ኢህአዴግ መደበኛ ጉባኤያቸውን በቅርቡ ያካሂዳሉ፡፡ በድርጅቱ ዲስፕሊን መሰረትም አዘጋጅ ኮሚቴዎች ተደራጅተው የቅድመ ጉባኤ ስራዎችን እያከናወኑ ቆይተው ለጉባኤዎቹ ዋዜማ ደርሰናል፡፡
ጉባኤዎቹ የባለፈው ጉባኤ ብቻ ሳይሆን ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ በህይወት በነበሩበት ወቅት በአዳማ በተካሄደው 8ኛ የትራንስፎርሜሽን ጉባኤ የታቀደው  የ5 አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አፈፃፀም ይገመግማል፣ የቀጣይ አምስት አመት ሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አቅጣጫዎች ይተልማል ተብሎ ይጠበቃል”” ስለሆነም በአባላቱ ብቻ ሳይሆን በመላው የሀገራችን ህዝቦች እና የአለም ማህበረሰብም ጭምር ትልቅ ትኩረት የሚሰጠው ጉባኤ ይሆናል””
ከጉባኤዎቹ ማግስት ስለጉባኤዎቹ ሂደትና ውሳኔዎች በወቅቱ በስፋት የምንዘግበው ሆኖ በዚህ እትም በብሄራዊ ድርጅቶች ያለፈው ጉባኤ በተወሰነው መሰረት የተከናወኑ እና የጉባኤ አጀንዳ በሚሆኑ ዋና ዋና ጉዳዮች ሰነድ አዘጋጅተው ሁሉም አባላት በየብሄራዊ ድርጅታቸው መወያየታቸው ይታወሳል፡፡ እኛም ሰነዶቹን መሰረት በማድረግ በዋናዋና ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ እንዲህ አጠናቅረነዋል፡፡ መልካም ንባብ፡፡

የትግራይ ክልል በህወሓት መሪነት

ህወሓት  እስከአሁን 11 ጉባኤዎች አካሂዷል፡፡ እስከ 10ኛ ጉባኤ የተካሄዱ ጉባኤዎች ሁሉ ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ የነበረባቸው ጉባኤዎች ነበሩና 11ኛ ጉባኤ የመለስ በመስዋእት መለየት በጉበኤው ላይ ከባድ ጥላ አጥልቶበት ነበር፡፡ ጉባኤው በመለስ መሪነት የተካሄደው 10ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ የወሰነው የአምስት አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን የ2 ዓመት ተኩል አፈፃፀም በመገምገም የነበሩ ጥንከሬዎችና ጉድለቶችን በመፈተሽ የመለስ እሴቶችን በመላበስና የመለስ ራእይን በመሰነቅ ዕቅዱን ለማሳካት ርብርብ እንደሚያደርግ በመወሰን ነበር የተደመደመው፡፡
እንደሚታወቀው የታላቁ መሪ ድንገተኛ ህልፈት በድርጅቱ፣ በህዝብና በወዳጆቻችን ትልቅ ድንጋጤን የፈጠረ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ነገርግን ድርጅቱ እንደለመደው ‹‹የጓዶቻችን መስዋእት ለህዝባዊ ዓላማዎቻችንና እቅዶቻችን መሳካት ተጨማሪ እልህና ቁጭት  ስለሚፈጥርልን የመለስ መስዋእትም አለምን የሚያስደምም ህዝባዊ ማእበል ይፈጥርልናል›› ብሎ በወሰነው መሰረት  ያገጠመውን የአመራር ጉድለት የሚሞላ አቅጣጫ በመቀየስ የትራንስፎርሜሽን እቅዱን ማሳከት ተችሏል፡፡

የገጠርና ግብርና ልማት

በትግራይ በተለይም የተፈጥሮ ሃብት ሰራዊት የተፈጠረውና የተገነባው የዛሬ አምስት አመት ነበር፡፡ ይህ የአንድ ግንባር ሰራዊት በክልሉ ለሚገነቡ ሌሎች የልማት ሰራዊት ግንባሮችና አሃዶች ብቻም ሳይሆን በሃገር ደረጀ በሁሉም ክልሎች የልማት ሰራዊት ለመገንባት እንደ ተሞክሮ ሆኖ ያገለገለ ነው፡፡ የተፈጥሮ ሃብት ሰራዊት ባለፉት አመታት በቀጣይነት እየተገነባና እየተጠናከረ በመምጣት በክልሉ የአፈር መከላትን መከላከልና የውሃ ማቀብ ስራው ሰፍቶ እፅዋቶችን ከብክነት በማዳን አከባቢው ወደሚድንበት ደረጃ ማድረስ መቻሉን የድርጅቱ የግምገማ ሰነድ አስረግጦ ገምግሟል፡፡ አርሶ አደሩም ከተፈጥሮ ሃብት ባገኘው ተሞክሮ በመነቃቃት ከመስኖ ልማት፣ ከእንስሳት ልማት እንዲሁም ከክረምት ምርታማነት ማሻሻያ ተግባራት በማስተሳሰር ተጠቃሚ መሆን ችሏል፡፡
በሰራዊት ልማት ግንባታው በአጠቃላይ የህዝቡ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ከመቻሉም በላይ በተለይም መሬት የሌላቸው ወጣቶችንና ሴቶችን እንዳይጠቀሙ ሲያደናቅፉ የነበሩ የተሳሳቱ ዝንባሌዎች ታርመው ተጠቃሚነታቸው ተሻሽሏል፡፡ በእርግጥ በዚህ በኩል ያለውን ኢንቨስትመንት ሙሉ በሙሉ ተከናውኗል የሚባል ስላልሆነ በሁለተኛ እድገትና ትራንስፈርሜሽን ትኩረት የሚሰጠው ይሆናል ጉባኤው ትኩረት ሰጥቶ ይወያይበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በክልሉ በተለይም ውሃ ህይወት ነው ያለ ውሃ የበጋም ሆነ የክረምት ልማት ማካሄድ አይቻልም የሚል ክልል አቀፍ መግባባት በእያንዳንዱ አርሶ አደር ድረስ መጨበጡ በክልሉ እያንዳንዱ አባወራ/ እማወራ ቢያንሰ ሁለት የውሃ ባንክ እንዲኖረው ተደርጓል፡፡ ስለሆነም የተፈጥሮ ሃብትን ሰራዊትን በእርሾነት ወስዶ በተደረገ ርብርብ ዛሬ የመስኖ ሰራዊትም ተገንብቷል፡፡
የክረምት ምርታማነት ንኡስ ግንባር ሰራዊትም በቴክኖሎጂ አጠቀቀምና በውጤት እንደየ አግሮ ኢኮሎጂ ወደ ተመጣጣኝ ደረጃ ለመድረስ ችሏል ስለሆነም የህዝብ፣ የመንግስትና የድርጅት ክንፍ ያጣመረ ሰራዊት መገንባት ተችሏል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ  ባለፉት አምስት አመታት በክልሉ አጠቃላይ የ10 ነጥብ 9 የኢኮኖሚ እድገት ተመዝግቧል፡፡ በክልሉም ኢኮኖሚው ባመነጨው መሰረት 11 ቢሊዮን ገቢ መሰብሰቡን እንመለከታለን፡፡ በዚህ መሰረትም ክልሉ 40 በመቶ በጀቱን ራሱ መሸፈን ወደሚችልበት ደረጃ ደርሷል፡፡

የከተማ ልማት አፈፃፀም

በትግራይ ከተሞች የሚታየውን  ሰፊ የድህነትና የስራ አጥነት ችግር ለመቅረፍ በሃገር ደረጃ የተቀረፀውን የጥቃቅንና አነስተኛ ስትራቴጂና ፓኬጅ መሰረት ከክልሉ ሁኔታ ጋር በሚጣጣም መልኩ በማቀድ ዘርፉ የከተማ ልማት መዘውር ሆኖ እንዲያገለግል ተደርጓል፡፡ በአለፉት አምስት አመታት 148 ሺህ 207 ኢንተርፕራይዞች ከተለያየ ደረጃ ከአንድና ሁለት ደረጃ የተሸጋገሩ መሆናቸውን እናያለን፡፡ በዚህም 20 ሺህ 324 የዩኒቨርስቲና ቴክኒክና ሙያ ምሩቃን በዘርፉ ተሳትፈዋል፡፡ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ የልማት ተቋማትን በጋራ በመተባበር ማሽነሪዎችን የሚያከራይ ተቋም እንዲያቋቁሙም ተደርጓል፡፡
ኢንቨስትመንት ለማበረታታትና ለባለሃብቶች ምቹ ሁኔታ መፍጠር የሚለው የ10ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ አንድ ውሳኔ ነበር፡፡ በዚህ መሰረት ባለፉት 5 አመታት በክልሉ በ11 ከተሞች 1337 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ ዋጋ ወጥቶለት ተዘጋጅቷል፡፡ ባለፉት አምስት አመታትም በክልሉ 47 ቢሊዮን ብር ካፒታል ያላቸው ኢንቨስትመንት ወደ ክልሉ ገብቷል፡፡ ከዚሁ ደግሞ 45 በመቶ በማኑፋክቸሪን ማለትም በከፍተኛና መለስተኛ ኢንዳስትሪ ኢንቨስት የተደረገ መሆኑ በስኬት የሚጠቀስ ነው፡፡
ክልሉ ምንም አይነት የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ከማይታይባቸው የሀገራችን ክፍሎች እንዱ እንደነበረ ይታወቃል፡፡ ነገርግን ደረጃ በደረጃ ኢንቨስትመንት ለመስፋፋት የክልሉ መንግስት ባደረገው ጥረት የዛሬ አምስት አመት 20 ቢሊዮን ደርሶ የነበረ ሲሆን በአለፉ አምስት አመታት በተደረገ ጥረት ግን  የ67 ቢሊዮን የኢንቨስትመንት አቅም ተፈጥሯል፡፡  በዚህ እና በሌሎች ስራዎች የክልሉን የድህነት መጠን ከ31. 8 በመቶ ወደ 22 በመቶ ማውረድ ተችሏል፡፡ የስራ አጥነት መጠኑም በተመሳሳይ ወደ 17 በመቶ ማውረድ ተችሏል፡፡

ማህበራዊ ልማት

ከ10ኛው ድርጅታዊ ጉባኤ ማግስት በትምህርት ልማት የተያዙ ሶስት ስትራቴጂካዊ ግቦች ነበሩ፡፡አንዱ የምእተ አመቱ ግብ ማሳካት ሲሆን ሁለተኛ መደበኛ ትምህርት ለሁሉም ሲሆን ሶስተኛ ደግሞ በ5 አመቱ እድገትና ትራንስፎርሜሽን የታቀዱ እቅዶችን ማሳካት ነበር”” በዚህ መሰረት በክልሉ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ቁጥር ወደ 2069፣ ሁለተኛ ደረጃ 146፣ መሰናዶ 76 ማድረስ ተችሏል፡፡አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ወዳለው ለመድረስ ወደ 2 ነጥብ 87 ኪሎሜትር ማድረስ ተችሏል፡፡ በዚህ መሰረት በአሁኑ ወቅት በክልሉ መማር ከነበረባቸው ህፃናት 88 በመቶ በትምህርት ገበታ ላይ ይገኛሉ፡፡ በሁለተኛ ደረጃና በመሰናዶም በእቅዱ መሰረት ሽፋኑ የተሳካ የነበረ ሲሆን ተግባር ተኮር የጎልማሶች ትምህርት ፕሮግራምም 2 ሚሊዮን 139 ሺህ 541 ጎልማሶች እንዲማሩ ተደርጓል፡፡
በክልሉ ሶስት ዩኒቨርስቲዎች የሚገኙ ሲሆን በሁለተኛው ትራንስፎርሜሽን እቅድ በደቡባዊ ዞን ተጨማሪ ዩኒቨርስቲ ለመስራት የመሰረት ድንጋይ መቀመጡ ይታወሳል፡፡
ጤናው የተጠበቀ አምራች የሰው ሃይል መኖር ለአንዲት ከድህነት ለመውጣት ለምትታትር ትግራይ ዓቢይ ጉዳይ ነው፡፡ እስከ 2007 በክልሉ የተገነቡ ጤና ጣቢያዎች 214 ሲሆኑ ይህም ለ25 ሽህ ህዝብ አንድ ጤና ጣቢያ የሚባለው መለስተኛ ግብ መሳካቱ እናያለን፡፡ ከዚህ በተጨማሪ 594 የጤና ኬላዎች በክልሉ ገጠር ቀበሌዎች ተገንብተዋል”” በቅድመ ወለድ ፣ በወሊድና ድህረወሊድ ክትትልና አገልግሎት ረገድ የምእተ አመቱ ግብ የሚያሳኩ ስኬቶች ተገኝተዋል፡፡ በ1996 በአንድ የፓርላማ ውሎ በወቅቱ የተጀመረው የውሃ ማቆር እንቅስቃሴ በመቃወም ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ‹‹አርሶ አደሩን በወባ ልትጨርሱት ነው›› ብለው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ሆኖም ዛሬ በክልሉ ቢያንስ አንድ የውሃ ባንክ የሌለው አርሶአደር ወደ ሌለበት ደረጃ እየተደረሰ ቢሆንም በአንፃሩ የወባ ስርጭት ወደ 4 ነጥብ 3 በመቶ በወባ ምክንያት ይከሰት የነበረው ሞትም ወደ 0.004 ማውረድ የተቻለበትና ወባ የአርሶ አደሩ ማህበረኢኮኖሚ ቀውስ የመሆኗ ጉዳይ ያከተመበት ደረጃ ላይ እንገኛለን፡፡

መሰረተ ልማት

በእቅድ ዘመኑ የክልሉ የመንገድ ሽፋን ርዝመት ወደ 7061 ኪሎሜትር ለማድረስ ታቅዶ የነበረ ሲሆን  አፈፃፀሙን ስንመለከት 6 ሺህ 433 ኪሎሜትር መሆኑን ያሳያል፡፡ እዚህ ለመድረስ በእቅድ ዘመኑ 4371 ኪሎሜትር መንገዶች መገንባታቸውን እንመለከታለን፡፡ በዚህ ጥረትም በክልሉ ከሚገኙ የገጠር ቀበሌዎች 576 ቀበሌዎች  በመንገድ ተገናኝተዋል”” በሌላ በኩል 400 የገጠር ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ ፍትሃዊ የልማት ስርጭቱ በተግባር ተተርጉሟል፡፡

Friday, 21 August 2015

አመራር አቅማችንን በቀጣይ በማጠናከር የከተማችንን ህዳሴ እናረጋግጥ! ይስሐቅ ግርማይ

አመራር አቅማችንን በቀጣይ በማጠናከር የከተማችንን ህዳሴ እናረጋግጥ!
በከተማችን ስር ሰደው የቆዩትን ድህነትና ኋላ ቀርነት በማስወገድ ልማትና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ርብርብ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡
ይህንኑ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት የአገራችን ይሁን የከተማችንን መሠረታዊ የህዝብ ጥያቄዎችን የሚመልሱ መስመሮችን፣ ስትራቴጂያዊ እቅዶችና ፖሊሲዎችን በማዘጋጀት በእንቅስቃሴ ላይ ነን”” ምልዓተ ህዝቡን በማንቀሣቀስም በለውጥ ሂደት ላይ እንገኛለን፡፡
ከተማችንን ጨምሮ በሀገር አቀፍ በ5 አመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመን በኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማት፣ በዴሞክራሲ ስርአት ግንባታና በመልካም አስተዳደር የተመዘገቡ ስኬቶች ከዚህ በፊት በተለያዩ ሰነዶች የቀረቡና የተወያየንባቸው በመሆኑ እዚህ ላይ መድገም አስፈላጊ አይደለም፡፡
 ነገር ግን አንድ መያዝ ያለበት ሀቅ በሁሉም ዘርፍ ያስመዘገብናቸው ድሎች የህዝቡ ተጠቃሚት ብቻ ሣይሆን የህዝብ ተሳታፊነት የተረጋገጠባቸው እንዲሆኑ ሰፊ የአደረጃጀትና አሰራር ዘርግተን ያከናወናቸው ነበሩ፡፡ ይህም ሆኖ ምንም እንኳን የተደራጀ የህዝብ አቅም አሟጠን ተጠቅመናል ለማለት ባንችልም የከተማችን ነዋሪዎች ከእቅድ ዝግጅት ጀምረው በሶስት ምዕራፎች ሚናቸው እያደገ እንደመጣ ግልፅ ነው፡፡
የህዝቡን እንቅስቃሴ የሚመራውና የሚያጠናክረው ደግሞ መሪ ድርጅት ነው፡፡ ይህ ሲባል ድርጅቱ የህዝቡን እንቅስቃሴ እየመራና በህዝቡ እንቅስቃሴ ውስጥ ድርጅታዊ ብቃቱንና ጥንካሬውን እያጎለበተ የሚሄድበትን የተሳሰረ ሁኔታ መፍጠር ወሣኝ የአመራር ተግባር ነው፡፡
በከተማችን ድርጅታችን ኢህአዴግ በህዝቡ ውስጥ ፖለቲካዊና ድርጅታዊ ስራዎችን እያከናወነ በየጊዜው ከህዝቡ እንቅስቃሴ ግንባር ቀደሞችን በመመልመል የድርጅቱን አቅም ለማስፋት ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡ የአባላችንን ግንባታም በተመሣሣይ ሰፊ ጥረት በማድረግ የውስጥ ድርጅት ፖለቲካዊ አቅሙን ለማሣደግ ሰፊ ጥረት ተደርጓል፡፡
ነገር ግን ይህንን ያህል ጥረት ተደርጎም አሁንም ቀላል የማይባል የማስፈፀም አቅም ችግር ይታያል፡፡ በከተማችን በህዝቡም ይሁን በአባሉ ዘንድ ያለው ዝንባሌ ኢህአዴግ የፖሊሲና ስትራቴጂ ችግር ሣይሆን የማስፈፀም አቅም ችግር አለበት የሚል ትችት ያቀርባል፡፡
ስለሆነም በአሁኑ ጊዜ እየተካሄደ ያለው ግምገማ እነዚህን ችግሮች ግምት ውስጥ በማስገባት የጠራ አመለካከት በመያዝ መሠረታዊ የአቅም፣ የስነ - ምግባርና የዝግጁነት ችግር ያለባቸውን አመራሮች የሚያጠራ መሆን ይኖርበታል፡፡
በከተማችን በአጠቃላይ ከ3 ሺህ 400 በላይ አመራር ያለ ሲሆን በእጅጉ ቁጥሩ እየጨመረ ያለውን አባላል በብቃት የሚመራና አቅሙ እያደገ የሚሄድ አመራር መፍጠር ወሣኝ ጉዳይ ይሆናል፡፡
የአመራር አቅማችንን የማሣደግ ጉዳይ በስልጠና ብቻ የሚከናወን ተግባር አይደለም፡፡ በማያቋርጥ የዕለት ተዕለት ተግባር ውጤታማ ስራዎችን ማከናወን ወሣኝ ነው፡፡ በተለይም በየደረጃው ካለው አመራር ለህዝብ ቅርብ ሆኖ ወሣኝ ሚና የሚጫወተው የወረዳ አመራራችን ሲሆን የውስጥ ፖለቲካዊ ትግል በማካሄድ መልሶ ማደራጀት ላይ ልዩ ትኩረት ሊደረግ ይገባል፡፡ በእርግጥ አመራርን የማጠናከር ጉዳይ በአንድ ወቅት ተሰርቶ የማይጠናቀቅ ቢሆንም ከቀጣይ ሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዳችን አንፃር ሲታይ አሁን መጀመሩ ትክክለኛና ተገቢ መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል፡፡
የወረዳ አመራራችን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ሲሆን ከቁጥሩ መስፋት ባሻገር አብዛኛው አመራር በድርጅት አባልነት ቆይታው አዲስ ነው፡፡ ስለሆነም የአመራር ተሞክሮና ልምድ የሚያንሰው መሆኑ የሚያከራክር ጉዳይ አይሆንም፡፡ ከዚህ አንፃር የአመራሩ አቅም በቀጣይ በተለያዩ ስልጠናዎችና በተግባር መገንባት ትኩረት ተሰጥቶት የሚፈፀም መሆን ይኖርበታል፡፡
ስለአመራር መጠናከር ሲታሰብ ሌላው ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ በየደረጃው ያለው አመራራችን የዴሞክራሲና የልማታዊ እሴቶችን መላበሱን በየጊዜው ክትትል ማድረግ ይገባል፡፡ የአመራራችን አቅም እንዲጠናከር ብቻ ሣይሆን አስተማማኝ የህዳሴ አመራር ሆኖ እንዲቀጥል ዴሞክራሲና ልማታዊ አስተሳሰብና ተግባርን የዕለት ተዕለት መመሪያዎቹ አድርጎ መንቀሣቀስ ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ተልዕኮ ሲፈፅምም በማናቸውም መስክ ሁሉ የዴሞክራሲና ልማታዊነት ባህሪ ይዞ ሲመራ ብቻ ነው፡፡
የዴሞክራሲ እሴቶች የሚባሉት በዋነኛነት የህግ የበላይነትን ማረጋገጥ፣ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ጥቅሞች የማስቀደም ሲሆን አመራሩ በዚህ ዙሪያ ግንባር ቀደምና አርአያ ሆኖ ራሱም ከተለያዩ የስነ ምግባር ችግሮች ፀድቶ መንቀሣቀስ ይጠበቅበታል፡፡
የልማታዊነት እሴት ሲባል ደግሞ ህዝቡ በልማቱ ተጠቃሚ እንዲሆን፣ በዚህ ሂደት እያንዳንዱ አመራር ህዝቡ ተጠቃሚ የሚሆንበትን ሁኔታ ለመፍጠር መንቀሣቀስና ጥረት ማድረግ አለበት፡፡ የራስን ጥቅም ከህዝብ ጥቅም አለማስቀደም ወዘተ የሚሉትን መሠረታዊ ባህሪያት መላበስን ከአንድ አመራር የሚጠበቅ ተግባር ይሆናል፡፡ ነገር ግን አመራራችን ከላይ ከተገለፁት ችግሮች የፀዳ አይደለም፡፡
ስለሆነም የዴሞክራሲና ልማታዊነት እሴትን የተላበሰ አመራር የመገንባት ጉዳይ በየደረጃው ያለው አመራር ከኪራይ ሰብሣቢነት አመለካከትና ተግባር የሚፀዳበትን ሁኔታ ተግባራዊ በማድረግ ሁሌም በኪራይ ሠብሣቢነት ላይ የሚደረገውን ትግል ትኩረት ልናደርግበት ይገባል፡፡
ጠንካራ አመራር የሚባለው ስራዎችን በዘፈቀደ ሣይሆን በታቀደው መንገድ የሚፈፅም መሆን አለበት፡፡ በአንድ ወቅት እንዲከናወኑ የሚፈለጉ በርካታ ተግባራት ይኖራሉ፤ ሁሉንም ተግባራት ግን በአንድ ጊዜና በተመሣሣይ ትኩረት መፈፀም አይቻልም፡፡ ስለሆነም አመራር ተግባራቱን እንደየ አንገብጋቢነታቸውና በሚኖራቸው ሚዛን ደረጃ በደረጃ በመመደብ ቁልፍ ተግባሩን ለይቶ የሚረባረብ መሆን ይኖርበታል፡፡
አመራሩ በማናቸውም ስራ ግንባር ቀደም መሆን የሚገባው ሲሆን ከሁሉም በላይ ደግሞ የራሱን ብቻ ተግባራት ጠቅልሎ በመያዝ ተልዕኮውን ሊያሣካ አይችልም”” የአመራር ብቃት አንዱና ወሣኙ ጉዳይ ሰርቶ የሚያሰራ መሆን ሲችል ነው”” ስለሆነም አመራሮች የሚመለከታቸው አካላት ወይም ሦስቱ የልማት ኃይሎችን በማብቃት ማንቀሣቀስ ይጠበቅበታል፡፡
ጠንካራ አመራር የሚባለው በድርጅትም ሆነ በመንግስት በተቀመጠው የክትትልና ድጋፍ ስርአት በአግባቡ መንቀሣቀስ የሚችል ነው፡፡ ይህ ሲባል ያልተጋነነ ሪፖርት የሚያቀርብ የበታች አካላትን ስራ በቅርብ የሚከታተልና ተገቢ ድጋፍ የሚሰጥ፣ ነገሮች ከመበላሸታቸው በፊት አስቀድሞ ዝንባሌዎችን እየተከታተለ አፋጣኝ መፍትሔ የሚሰጥ ሲሆን ነው፡፡
በየደረጃው ያለው የአመራር ጥንካሬ የሚለካው ከሁሉም በላይ ባስመዘገበው ውጤት ነው፡፡ ከስራ ውጤት ውጭ የሚኖር ማናቸውም አይነት ሚዛን ተጨባጭነት የሌለው ለተለያዩ አዝማሚያዎች የተጋለጠ መሆኑ የማይቀር ሀቅ ነው፡፡
ስለሆነም በአሁኑ ጊዜ በየደረጃው የሚካሄደው የአመራር ግምገማ ስራዎቹ በዝርዝር እየተቆጠሩ፤ የእያንዳንዱ ተግባር አፈፃፀም በዝርዝር እየተገመገመና በስነ - ምግባር የተመሰገኑና ችግር ያለባቸው የሚለዩበትን ስርአት ተግባራዊ በማድረግ እንደአካልም ሆነ እንደ ግለሰብ በውጤቱ የሚታወቅበት ሁኔታ መፈጠር ይኖርበታል፡፡
በኮሚቴ ስም በጅምላ ጠንካራ ወይም ደካማ እየተባለ የሚታለፍበት፣ የጎላ ስነ ምግባር የሌለበትና በኪራይ ሰብሣቢነት ተግባር የገባ በድምፅ ብልጫ እየተባለ ጥገኝነት የሚጠናከርበት ሣይሆን እያንዳንዱን ግለሰብ በአብዮታዊ ስነ ምግባሩና በስራ ውጤቱ በመመዘን ውሣኔ የሚሰጥበትን አሰራር በማዳበር የከተማችንን የለውጥ ህዳሴ አመራር ማጠናከር ወሣኝ ተግባር ይሆናል፡፡


ድልና ድምቀት ለብሄራዊ ድርጅቶቻችንና ለኢህአዴግ ጉባኤ!!


ብሄራዊ ድርጅቶቻችንና የጋራ ግንባራችን የሆነው የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር/ኢህአዴግ/ ከነሐሴ አጋማሽ ጀምረው መደበኛ ድርጅታዊ ጉባኤያቸውን ያካሂዳሉ፡፡ የድርጅታችን ጉባኤ ከውስጠ ድርጅት ጉዳዮች ባለፈ በምርጫ ስልጣን ይዞ መንግስትን እንደሚመራ ድርጅት መጠን ትላልቅ ሃገራዊ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማት፣ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች የሚመከሩበትና ለቀጣይ አመታት አቅጣጫዎች የሚቀመጡበት ውሳኔዎች የሚወሰኑበት በመሆኑ ትልቅ ሃገራዊ ክንውን ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
እስከ አሁን በተደረጉት ጉባኤዎች የተወሰኑ ውሳኔዎች በኢትዮጵያ ህዳሴ ጉዞ የየራሳቸው አሻራ ያሳረፉ ታሪካዊ ክንዋኔዎች በመሆናቸውና የድርጅታችን ጉባኤዎች ለይስሙላና የግዜ ሰሌዳውን ጠብቆ መካሄድ ስላለባቸው ብቻ የሚካሄዱ ሳይሆኑ እንደድርጅትና እንደሃገር ከአንድ ምዕራፍ ወደ ሌላ ምዕራፍ ለመሸጋገር የሚያስችሉ መሆናቸው እስከአሁን ከተካሄዱት ጉባኤዎች መላው ህዝባችን የድርጅታችንና የሃገራችን ወዳጆችና ከድርጅታችን የተለየ አቋም ያላቸው ሃይሎች ጭምር የሚገነዘቡት ሐቅ ነው፡፡
ስለሆነም በነሐሴ ወር ‹‹ህዝባዊ አደራን በላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን›› በሚል መሪ ቃል የሚከናወነው የኢህአዴግ ጉባኤ እንዳለፉት ጉባኤዎቻችን ሰፋፊ ሃገራዊ እቅዶችንና የሃገራችንን የልማትና የዴሞክራሲያዊ ስርአት ተጨማሪ ድልና መደላድል የሚፈጥሩ ውሳኔዎች እንደሚያስተላልፍ ይጠበቃል፡፡
 የብሄራዊ ድርጅቶቻችንም ሆኑ የኢህአዴግ ጉባኤ ባለፉት አምስት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዓመታት የመድረኩን ተልእኮ ለመፈፀም ድርጅታዊ የአመራር አቅም በማጠናከር፣ የህዝብ ተሳትፎ ከመቼውም በተለየ በማደራጀት፣ እንዲሁም አገልግሎት የሚሰጠው ሲቪልሰርቪሱም የተልእኮውን ፖለቲካዊ አላማና ግብ ተገንዝቦ እንዲተጋ አደራጅቶ በመምራት የልማትና የመልካም አስተዳደር እንዲሁም የምርጫ ተግባራትን ለማሳካት ሰፊ ጥረት የተደረገበትና በሁሉም እቅዶች ስኬቶች በተመዘገቡበት ወቅት የሚካሄዱ በመሆናቸው የድል ጉባኤዎች ናቸው፡፡
እንደ ግንባር በሃገር ደረጃ እንዲሁም ብሄራዊ ድርጅቶቻችን በየክልሉ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዘመኑ የታቀዱና የተጣሉ ግቦችን ለማሳካት በተደረገው ርብርብ አብዛኛዎቹ ተግባራት በግቡና ከግቡ በሚቀራረብ ደረጃ መሳካታቸው የሁለተኛው 5 አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዶችን በተለጠጠ ግብ ለማቀድና እንደሃገርና እንደድርጅት የይቻላል በራስ መተማመናችን ከመቸውም ጊዜ በላይ በላቀ ደረጀ በሚገኝበት ወቅት ሆነን የምናካሂደው ጉባኤ ነው፡፡፡
የግቦቹ ዋና ማሳኪያ መሳሪያ የተደራጀ የድርጅት፣ የመንግስትና የህዝብ አቅም መሆኑ በተያዘው አቅጣጫ መሰረት ባለፉት ሁለት አመታት የሰራዊት ግንባታ ዋናው የአቅም ግንባታ ማእከል በማድረግ በተሰራው ስራ የሰራዊቱ ፈፃሚ አቅሞች እቅዶችን በማሳካት ረገድ የነበራቸው ብቃት እንደድርጅት መመዘን በሚቻልበት ወቅት ላይ ሆነን  የምናካሂደው ጉባኤ ነው፡፡
የዘንድሮ ጉባኤ የዛሬ አምስት አመት የመጀመሪያው አምስት አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ሲታቀድ እቅዱን በማቀድና እቅዱ በድርጅቱና በህዝብ ዘንድ ጠንካራ መግባባትና መነሳሳት እንዲፈጠር ወሳኝ ድርሻ የነበረው ታላቁ መሪያችን መለስ ዜናዊ በሌለበት ነገርግን በተሰዋበት ወቅት የድርጅታችን አመራር የተፈጠረውን የአመራር ክፍተት መሙላት የሚያስችል የአመራር ስልት በመቀየስ ጠቅላላ የድርጅቱ አባላት፣ የመንግስት መዋቅሩና ህዝቡን አደራጅቶ በማነቃነቅ የመለስን ራእይ ማሳካት እንደሚቻል በተረጋገጥንበት ወቅት የሚካሄድ መሆኑም ልዩ ያደርገዋል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በሰራዊት ግንባታ ከክልል ክልል፣ በገጠርና በከተማ፣ በሴክተሮችና በህዝብ አደረጃጀቶች እንዲሁም በድርጅቱ ውስጥም ሰፊ የሆነ አለመመጣጠን እንደሚታይበት ይታወቃል፡፡ ከህዝብ ተጠቃሚነት አንፃርም በአለማችን እየተገነቡ ካሉት ኢኮኖሚዎች በየትኛውም መመዘኛ ሲመዘን ፍትሃዊና የአብዛኛው ህዝብ ተጠቃሚነትና ተሳታፊነት ያረጋገጥንበት እንደነበረ የመጀመሪያው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን አፈፃፀም ያሳያል፡፡ ይህም ሆኖ በዚህ በኩል ያለው ስራ ገና ያልተጠናቀቀና ከአካባቢ አካባቢ የአፈፃፀም ልዩነቶች የሚታይበት መሆኑ አልቀረም፡፡ ስለሆነም በዚህ ዙሪያ የተገኙ ስኬቶችን በመቀመር ጉድለቶችን ማረም የሚያስችሉ አቅጣጫዎች ከጉባኤው ይጠበቃል፡፡
በተሃድሶ ወቅት የስርአታችን አደጋ ኪራይ ሰብሳቢነት መሆኑ እና ይህም ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረቶች ያሉት መሆኑ በተቀመጠው መሰረት የኪራይ ሰብሳቢነት ፖለቲካል ኢኮኖሚው በልማታዊ ዴሞከራሲያዊ ፖለቲካል ኢኮኖሚ ለመቀየር የሞት ሽረት ትግል ሲካሄድ ቆይቷል”” በአሁኑ ወቅት በሀገራችን ገጠሮች በተገነባው የልማት ሰራዊት የኪራይ ሰብሳቢ ፖለቲካል ኢኮኖሚ ሙሉ በሙሉ የተሸነፈበት ደካማ መሬት ይዞ የሚንገዳገድበት ደረጃ ላይ እንገኛለን፡፡  ይህም ሆኖ አሁንም በገጠርም ጭምር ለኪራይ ሰብሳቢነት ማዳበሪያ የሆኑ የጠባብነትና የትምክህት በሽታዎች ሙሉ በሙሉ ተመምግለው ተወግደዋል የሚባሉበት ደረጃ አልተደረሰም፡፡ ስለሆነም የብሄራዊ ድርጅቶቻችንና የኢህአዴግ ጉባኤ በገጠር ከኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብና ተግባር ያልተወገዱ ቅሪቶችን በቀጣይ አምስት አመታት ጨርሰው የሚከስሙበት አቅጣጫ ያስቀምጣል ብለን እንጠብቃለን፡፡
በከተሞቻችን አዲስ አበባን ጨምሮ የነበረው የገነገነ የኪራይ ሰብሳቢ ሃይል የተደራጀ አቅምና ስብስብ የማድረግ አቅሙ እጅግ በተዳከመ ደረጃ ላይ መድረሱ በ2007 በተካሄደው አምስተኛው ሃገራዊ ምርጫ የኪራይ ሰብሳቢ ጠበቃ የሆኑ ፅንፈኛ ፓርቲዎች የተከናነቡት ሽንፈት ማረጋገጫ ነው፡፡ ይህም ሆኖ በከተማ የተገነባው የልማት ሰራዊት በገጠር የተገነባው የልማት ሰራዊት የደረሰበት የአደረጃጀትና የአስተሳሰብ ጥራት አንፃር ሲመዘን ብዙ ጉድለቶች ያሉበት በመሆኑ የኪራይ ሰብሳቢነት ፖለቲካል ኢኮኖሚ በሚፈለገው ደረጃ የተደፈቀበት አይደለም፡፡ በመሆኑም በከተሞች በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመን እንደገጠሩ ሁሉ መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት መደላድል የሚፈጥሩ የኢኮኖሚ፣የማህበራዊና የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታ የተከናወነ ቢሆንም በዛው ልክ የአስተሳሰብ ለውጥ እንዳይመጣ በመልካም አስተደደር በተለይም በአገልግሎት አሰጣጥ ያለው ጉድለት ከፍተኛ አሉታዊ ሚና ተጫውቷል፡፡
ከገጠር በተገኘው ልምድ ካለ ጠንካራ የድርጅት፣ የመንግስትና የህዝብ የተቀናጀ የልማት ሰራዊት ኪራይ ሰብሳቢነትን መድፈቅና መልካም አስተዳደር ዘላቂነት ባለው ደረጃ ማረጋገጥ አይቻልም፡፡ ስለሆነም የድርጅታችን ጉባኤ በዚህ ረገድ ያለውን ጉድለት በጥልቀት ተወያይቶ የከተማ የልማት ሰራዊት ግንባታ፣ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ እንዲሁም የእድገት ፀር በሆነው የኪራይሰብሳቢነት ትግል ላይ እመርታዊ ለውጥ ማምጣት የሚያስችሉ ውሳኔዎችንና አቅጣጫዎችን ያመነጫል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በአጠቃላይ ዘንድሮ የሚካሄደው የድርጅቶቻችን ጉባኤ የድል ጉባኤ ነው፡፡ በኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማት ለተመዘገበው ሃገራዊና ክልላዊ እድገት የሚመጥን ድምፅም ህዝቡ በአምስተኛው ሃገራዊ ምርጫ ለድርጅታችን ሰጥቷል፡፡ ነገርግን ህዝቡ ከመቼውም ጊዜ በላቀ ድምፅ ኢህአዴግን መምረጡ እስከአሁን ለሰራቸው ስራዎች እውቅና ብቻ ሳይሆን እስከአሁን በሁሉም ዘርፍ ከተመዘገቡ ድሎች በላይ የላቀ ሃገራዊ እድገት እንዲመዘገብ ብቁ አመራር እንዲሰጠው የሰጠው አደራና ሸክም በመሆኑ የጉባኤው ፋይዳና በጉባኤው የሚተላለፉ ውሳኔዎች በሁሉም ዘንድ በከፍተኛ ትኩረት የሚጠበቅ አድርጎታል፡፡ ለዚህም ነው የጉባኤው መሪ ቃል ‹‹ ህዝባዊ አደራን በላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን›› እንዲሆን የተመረጠው፡፡ በትክክልም ጉባኤው ህዝባዊ አደራን በላቀ እድገትና ትራንስፎርሜሽን ለመወጣት ድርጅታችን የአመራር ድርጅታዊ ጥንካሬና ዝግጁነት ያለው መሆኑን የሚያረጋግጥበት ጉባኤ ይሆናል፡፡

ድልና ድምቀት ለብሄራዊ ድርጅቶቻችንና ለኢህአዴግ ጉባኤ!!

Thursday, 6 August 2015

አንፀባራቂ ድሎቻችን በመጠበቅ ለቀጣይ ከባድ ህዝባዊ ኃላፊነት በቁርጠኝነት እንነሳ!!

ህዳሴ ጋዜጣ

 
መጀመሪያውን ዙር የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አጠናቀን በደማቅ አገራዊ ምርጫ ድል ታጅበን ወደ ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በመሸጋገር ላይ እንገኛለን”” በተግባር ላይ የዋለው የመጀመሪያው ዙር የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በሁሉም መስኮች አንፀባራቂ ድሎች የተመዘገቡበት ሂደት የነበረ ሲሆን ወደ ፊት ሊቀረፉ የሚገባቸው ውስንነቶችም ነበሩት፡፡
በመጀመሪያ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመን መጨረሻ አምስተኛው ዙር አገራዊ ምርጫም ስለተካሄደ ጥንካሬዎቻችንና ድክመቶቻችን በህዝባችን እይታ ፍንትው ብለው እንዲወጡ ያደረገና መላው የከተማችን ነዋሪዎች በዴሞክራሲያዊ ምርጫ በካርዳቸው የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ የተሃድሶ መስመራችንን ቀጣይነት አረጋግጠዋል፡፡ ይህ ለድርጅታችን ኢህአዴግ ትልቅ ስኬትና ከባድ ኃላፊነትም ነው፡፡ በመሆኑምለ2008 እቅድ ዓመት ብቻም ሳይሆን ለሁለተኛው የእድገትና ትራንሰፎርመሽን እቅድ ዘመን ጥንካሬዎቻችንን እና ድክመቶቻችንን ገምግመን ጥንካሬዎቹን ይበልጥ ለማጎልበት ድክመቶቻችንን ለማረም የሚያስችል ትምህርት መውሰድና ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡
 
1/ የኢህአዴግ የተሃድሶ መስመር ምሰሶዎች ፣ የከተማ አስተዳደሩ
  ራዕይ ተልእኮና የህዝባችን ፍላጎት
 
የተሃድሶ መስመራችን ምሰሶዎች ልማት፣ ዴሞክራሲና መልካም አስተዳደርን ማረጋገጥ ነው”” እነዚህ ዓላማዎች እየተሳኩ ሲሄዱ አስተማማኝ ሰላም እየተረጋገጠ ይሄዳል ተብሎ ይታመናል፣ ሰላም የልማትና የመልካም አስተዳደር መነሻም ውጤትም ሊሆን ይችላል፡፡ ለማልማት አስተማማኝ ሰላም ያስፈልጋል ልማትና የህዝብ ተጠቃሚነት ካለ ደግሞ አስተማማኝ ሰላም ይኖራል፡፡ ስለዚህ አንዱ የሌላኛው መነሻ ወይም ውጤት በመሆን በተመጋጋቢነት እየተጠናከረ ስለሚሄድ ሰላም የልማት፣ የዴሞክራሲና የመልካም አስተዳደር አካል ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
 ልማት ስንል በተሃድሶ መስመራችን አቅጣጫ መሰረት ፈጣን፣ ቀጣይነት ያለው ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ልማትና እድገት እንደሆነ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ ይህ ማለት ልማትና እድገት ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ፈጣን ካልሆነና ቀጣይነት ከሌለው ለመገመት የሚያስቸግር አደጋ ሊገጥመን ይችላል ማለት ነው፡፡ እድገት ኖሮ ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ካልሆነ ሰላም አይኖርም፣ ጤናማ እድገት አይሆንም ማለት ነው፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ ድርጅታችን ኢህአዴግ ፈጣን፣ ቀጣይነት ያለው፣ ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ልማትና እድገት የማረጋገጥ ግልጽ የልማት አቅጣጫ በተሃድሶ መስመራችን አንጥሮ በማስቀመጥ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡
ከተማችን አዲስ አበባ በ2017 መካከለኛ ገቢ ካላቸው ከተሞች ጋር ተወዳዳሪ የሆነች፣ ለኑሮና ለስራ ምቹና የመልካም አስተዳደር ተምሳሌት እንድትሆን የማድረግ ራዕይ አንግቦ ሰላም የማረጋገጥ ፈጣን፣ ቀጣይነት ያለውና የከተማችን ህዝብ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ልማት የማረጋገጥ ዴሞክራሲና መልካም አስተዳደር የማስፈን ተልእኮ ለማሳካት እየተረባረበ ይገኛል፡፡ በዚህ መሠረት በተሃድሶ መስመራችን ከተቀመጠው አቅጣጫና በመጀመሪያው ዙር የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ከተቀመጡት ግቦች አንፃር ያለንበት ደረጃ ምን ይመስላል? ሊጠናከሩ የሚገባቸው ስኬቶችና በፍጥነት ሊታረሙ የሚገባቸው ክፍተቶችን ጠቅለል ባለ መልኩ እንደሚከተለው ለማንሳት ተሞክሯል””
 
2/ ባለፉት አምስት አመታት የተገኙ ድሎች
 
ከተሃድሶ በኋላ  በአገር ደረጃ ልማት፣ መልካም አስተዳደር፣ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ድሎች እንደተጠበቁ ሆነው በመዲናችን አዲስ አበባም በተለይም ባለፉት አምስትና ስድስት ዓመታት ፈጣን የልማትና እድገት ግስጋሴ እየታየ መሆኑ ዓለም የመሰከረለት ሃቅ ሆኗል፡፡ በቤቶች ልማት ረገድ የከተማ አስተዳደራችን ከ136,000 በላይ ቤቶች ለተጠቃሚ በማስተላለፍ ከ 675,000 ህዝብ በላይ ተጠቃሚ ያደረገ ስኬታማ የቤት ልማት ኘሮግራም እየተካሄደ ይገኛል፡፡ የቤት ልማት ኘሮግራማችን የመጠለያ ችግርን ከመፍታት ባሻገር የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪውን በማሳደግና የስራ እድል በመፍጠር እንዲሁም ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል በማረጋገጥ ረገድ ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል፡፡
በከተማችን ባለፉት አምስት ዓመታት ሲካሄድ በቆየው መጠነ ሰፊ የስራ እድል ፈጠራና የኢንተርኘራይዞች ልማት ኘሮግራም በዕቅድ ዘመኑ ለ735,772 ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር የኑሮ ውድነትን ከመቋቋም አኳያ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል፡፡ ከኢንተርኘራይዞች ልማት አንፃር የማደራጀት፣ የማሰልጠን፣ የብድር አቅርቦት፣ የገበያ ትስስር፣ በቴክኒክና ሙያ የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ድጋፍ በመስጠት፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ደግሞ የድጋፍ አሰጣጡን ለማጠናከር በ 114 ወረዳዎች የአንድ ማእከል አገልግሎት ማደራጀት ተችሏል፡፡ በዚህም በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ የከተማችን ወጣቶችና ሴቶች ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ በዚህ ዘርፍ ያለው ችግር የድጋፍና ክትትል አሰጣጥ ስርዓቱ ደካማ ስለሆነ መስተካከል አለበት፡፡
በከተማችን ከተመዘገቡት አመርቂ ውጤቶች አንዱ በመሰረተ - ልማት የመጣው አስደናቂ ለውጥ ነው፡፡ የመንገድ ልማት ሽፋኑን ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ ከ 9.2 በመቶ ወደ 20.1 በመቶ በማሳደግ ከፍተኛ ውጤት ተመዝግቧል፡፡ የከተማችንን የውሃ አቅርቦት ችግር ለመፍታት በተደረገው ርብርብ በቀን የሚመረተውን የውሃ መጠን ከ 265 ሺህ ሜትር ኪዩብ በእቅድ ዘመኑ መጨረሻ ወደ 599 ሺህ ሜትር ኪዩብ በማሳደግ ሽፋኑን ከ 64 በመቶ ወደ 90 በመቶ ማድረስ ተችሏል፡፡ በዚህም ተቋም ያለው ዋናው ችግር የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓቱ ደካማ በመሆኑ መስተካከል አለበት”” በመንገድ ግንባታ ሂደት የነበሩ መጓተቶችን፣ የጥራትና የቅንጅት ችግሮችንም በተመሰሳይ በቀጣይ መፍታት አለብን””
በማህበራዊ ልማት ዘርፍ፣ የትምህርት ተደራሽነትና ጥራትን ለማሳደግ የተደረገ ጥረትና የተገኘው ውጤት፣ ሞዴል ትምህርት ቤቶች የመፍጠር እንቅስቃሴና አበረታች ውጤን ማሳየቱ፣ ቀጣይነት ያለው ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት መረጋገጡ በስኬት የሚገለፅ ነው፡፡ በጤና ልማት በኩልም በአብዛኛው ወረዳዎች ጤና ጣቢያዎች በመገንባትና ነባር ሆስፒታሎችንም በማስፋፋት የጤና ሽፋን አገልግሎቱ መቶ በመቶ መድረሱ፣ የእናቶችና ህፃናት ሞት በከፍተኛ ደረጀ መቀነሱ፣ ሴቶች በልማት ቡድን ተደራጅተው የጤና ልማት ባለቤት መሆን መጀመራቸውን እንመለከታለን”” ከዚህም በተጨማሪ የወጣት ማእከላት መስፋፋታቸው፣ የጎዳና ተዳዳሪን ወጣቶችን ስራ ማስያዝ፣ ወላጅ አልባ ህፃናትን መንከባከብ፣ አረጋውያንን መንከባከብ፣ አካል ጉዳተኞችን መንከባከብ መጀመራችን በማህበራዊ ልማት ከተገኙ ስኬቶቻችን መካከል ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ በዚህ ዘርፍ ያሉ የስራ ጥራትና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች እንደየተቋሙ መገለጫና ባህሪ ተገምግመው አንድ በአንድ መስተካከል ይገባቸዋል፡፡
ባለፉት ዓመታት የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከቶችና ተግባራትን እየታገልን ገቢያችን ከዓመት ዓመት እያደገ እንዲመጣ በማድረጋችን፣ ከበጀታችን የካፒታል ወጪ በአማካይ 66 በመቶ እንዲይዝ በማድረግ የከተማችን ልማት በፍጥነት እያደገ እንዲመጣ አድርጓል፡፡
ከፍ ሲል በተገለፁና በሌሎች ተጨማሪ ምክንያቶች የከተማችን አማካይ የእድገት ምጣኔ ከአጠቃላይ አገራዊ አማካይ የእድገት ምጣኔ በላይ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ የድህነት ደረጃው በመጀመሪያው የእቅድ ዘመን ከነበረበት 28.1 በመቶ ወደ 26 በመቶ ወርዷል”” በ2007 መጨረሻ የድህነቱ ደረጃ ወደ 22 በመቶ እንደሚወርድ ተገምቷል፡፡ የስራ አጥነት ምጣኔው ከነበረበት 27.9 በመቶ ወደ 23 በመቶ ወርዷል፡፡ (ይህ ስሌት የ2007ትን ተጨማሪ መረጃ አይጨምርም)፡፡ ይህ እውነታ የሚያሳየው ነገር ቢኖር የተሃድሶ መስመራችን፣ ፖሊሲያችንና ስትራቴጂያችን የህዳሴ ጉዟችንን በአስተማማኝ ሁኔታ እየመራና እያፋጠነ መሆኑን፣ የከተማችን አስተዳደርም ተልእኮውን ከመወጣት አንፃር አበረታች ውጤቶች እያስመዘገበ መሆኑን ያመለክታል፡፡
 
3/ የ2007 ሃገራዊ ምርጫ ምን ይነግረናል?
 
የዘንድሮው ሃገራዊ ምርጫ በባህሪው ለየት ያለ ነበር፡፡ በአንድ በኩል የኒዮ-ሊበራል አሽከሮች የተሃድሶ ጉዟችንን በመቀልበስ ከተቻለ ለማሸነፍ ካልተቻለ ለመበጥበጥ ከቅድመ ምርጫ ጀምረው ሰፊ ርብርብ ያካሄዱበት፤ በሌላ በኩል አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ድርጅታችን የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመራችንን ቀጣይነት ለማረጋገጥ የተፋለመበት ምርጫ ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር ምርጫው የተመራበት አግባብ ለቀጣይ ስራዎቻችን ምን ትርጉም ይኖረዋል? ምን ትምህርት እንወስዳለን? ምን አይነት ድምዳሜዎች ማስቀመጥ እንችላለን? የሚሉ ነጥቦችን በሚመልስ መንገድ አጠር አድርጎ ማየቱ ጠቃሚ በመሆኑ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
 
 - በጠራ ስትራቴጂ፣ እቅድና ጥብቅ የአመራር  
  ዲሲኘሊን ግቦቹን ያሳካ ደማቅ ፍፃሜ
 
ምርጫው በጠራ ስትራቴጂና እቅድ የተመራ ነበር፡፡ ስትራቴጂው የ2002 ምርጫን መነሻ ያደረገ ሆኖ ግልፅ ህሊናዊና ነባራዊ የሁኔታ ግምገማ፣ የሃይሎች አሰላለፍ፣ ስትራቴጂካዊ ግቦች፣ መሠረታዊ የማስፈፀሚያ አቅጣጫዎችን የመለሰ ነበር፡፡ ስትራቴጂውን ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችል በየደረጃው ጥራት ያለው እቅድ እንዲዘጋጅ ተደርጓል፡፡
አመራሩና መዋቅራችን ከጅማሬው የስራ ክፍፍል በማድረግ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራን የሚመራና የምርጫ ስራን የሚመራ ብሎ በማደራጀት እርስ በርሱ እየተመጋገበ በጋራ ኮሚቴዎችና ራሱን ችሎ በምርጫ ኮሚቴ የከተማና ክ/ከተማ የጋራ መድረክ በየሳምንቱ እየገመገመ፣ ልምድ እየተለዋወጠ፣ ችግሮችን እየለየና መፍትሄዎችን እያስቀመጠ በጥብቅ ዲሲኘሊን የተመራበት አግባብ ለቀጣይ ስራዎቻችን ምሳሌ የሚሆነን ነው፡፡
አባሉም ምርጫው በስኬት እንዲጠናቀቅ በእቅድ ከመመራት ጀምሮ፣ ራሱን፣ ቤተሰቡንና የቅርብ ጎረቤቱን በፍጥነት የምርጫ ካርድ እንዲወስድ በማድረግ፣ በኔትወርክ አማካይነት የድርጅታችንን የምርጫ መልዕክቶች በአፋጣኝ እንዲተላለፉ በማድረግ፣ አፍራሽ የቅስቀሳ ጽሁፎችንም ሆነ መልዕክቶችን ሲያይ ለሚመለከተው አካል በፍጥነት የማስተላለፍና በአመለካከት የመታገል፣ በድምፅ መስጫው ዕለትም በስሩ የያዛቸውን መራጮች በነቂስ በማውጣት ምርጫው ቀድመን በያዝናቸው ግቦች መሰረት እንዲጠናቀቅ የተጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደነበር መውሰድ ይቻላል፡፡
በውጤቱም ምርጫው ከጅማሬው እስከ ፍፃሜው ሰላማዊ፣ ነፃና ፍትሃዊ፣ ዴሞክራሲያዊ፣ በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያተረፈና በሚያስገርም ሁኔታ በሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች ኢህአዴግ በአሸናፊነት በማጠናቀቅ የምርጫ ግቦቻችን ሙሉ በሙሉ የተሳኩበት ደማቅ ፍፃሜ ሆኖ ተጠናቋል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በምርጫው ሂደት የታዩ የተለያዩ ክፍተቶችም ነበሩ፡፡ በእቅድ ዝግጅት እስከ ወረዳ በተሻለ ደረጃ የተዘጋጀ ሲሆን የታችኛው መዋቅር ላይ የግል እቅድ ግን መጓተትና መንጠባጠብ እንዲሁም የጥራት ችግር ነበረበት፡፡ በመራጮች ምዝገባ ሂደትም ከተሰጠ አቅጣጫ ውጪ የመስራትና ለማስመዝገብ የመፈለግ አልፎ አልፎ የታየ ጉድለት ነበረ፡፡ ይህ ለቀጣይም ትምህርት ሊወሰድበት ይገባል፡፡
 
 -የተሃድሶ መስመራችን ቀጣይነት በምልአተ  
  ህዝቡ ይሁንታ ያገኘበት ምርጫ
 
ህዝባችን የተጀመረው ፈጣን የለውጥ ጉዞ እንዲቀጥል ካለው ፅኑ ፍላጎት በመነሳት 2007 ምርጫ ከምርጫ 2002  በበለጠ ይሁንታውን የሰጠበት ስኬታማ ምርጫ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ነገርግን ያስመዘገብናቸው ድሎች እንደተጠበቁ ሆነው የልማት ፍሬዎችን ማጣጣም የጀመረና በከፍተኛ ደረጃ ለውጥ ፈላጊ ህብረተሰብ በመፍጠራችን እንዲሁም ያልተፈቱ የመሰረተ-ልማት ችግሮች ማለትም እንደ ውሃ፣ መብራት፣ ትራንስፖርት ያሉ በኛ የአፈፃፀም ጉድለት ምክንያት የሚፈጠሩ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችም እያሉ ኢህአዴግ የራሱን ችግሮች በራሱ የማረም ባህል አለው በሚል እምነት ከነጉድለታችን ይሁንታውን እንደሰጠን መገንዘብ ይገባል፡፡
ከምርጫ 2007 የምንወስደው መመረጣችንን ብቻ ሳይሆን ህዝባችን ምን ያህል ከባድ ኃላፊነት እንዳሸከመንና ኃላፊነታችንን ለመወጣት ከፍተኛ ዝግጅት ማድረግ እንዳለብን ጭምር ነው”” ለዚህም ነው ድርጅታችን ኢህአዴግ ከምርጫ 2007 ማግስት ጀምሮ ሁለተኛ ዙር የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አዘጋጅቶ ህዝቡን ወደ ማወያየት የገባው፡፡ በቀጣይ የህዝቡ ግብአት ታክሎበት ዳብሮ ከፀደቀ በኋላ በቀጥታ ወደ ስልጠናና ትግበራ የሚገባ ይሆናል፡፡ ስለዚህ አመራራችንና አባላችን ህዝቡ የሰጠንን ኃላፊነት በብቃት ለመወጣት የተሟላ ህዝባዊ ተነሳሽነት፣ ስነ-ምግባርና ሁለገብ ዝግጁነት ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡
 
 - የዜሮ ድምር የነውጥ ፖለቲከኞችን  
  በዴሞክራሲያዊ መንገድ ያሰናበተ ምርጫ
 
2002 ዓ.ም በተካሄደው 4ኛ ዙር አገር አቀፍ ምርጫ ኢህአዴግ ተቃዋሚዎችን በዝረራ ማሸነፉ የአውራ ፓርቲ እውን መሆንና ከፍ ወዳለ አዲስ ምዕራፍ መሸጋገራችንን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትራችን መለስ ዜናዊ በምርጫው ማግስት በሐምሌና ነሃሴ 2002 በታተመው አዲስ ራዕይ መጽሔት ባወጣው ፅሁፍ ገልፆ ነበር። ይህ እውነታ የተፃፈው ኢህአዴግ ለቀጣይ ተከታታይ ምርጫዎች በከፍተኛ ድምፅ በማሸነፍ በአውራ ፓርቲነት ሊቀጥል እንደሚቻል ታሳቢ በማድረግ ነበር።
በ2007 አገር አቀፍ ምርጫም ኢህአዴግ ከ2002 አገራዊ ምርጫ በተሻለ ደረጃ ሙሉ በሙሉ በማሸነፍ የአውራ ፓርቲነት ቦታውን አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡ የዜሮ ድምር የነውጥ ፖለቲከኞችን ህዝቡ በዴሞክራሲያዊ መንገድ ጥግ አስይዞ ሸኝቷቸዋል። ይህ የሚያሳየው ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ የተሃድሶ መስመራችን ምን ያህል ስር እየሰደደ እንደሆነና ህዝቡን በየደረጃው ተጠቃሚ እያደረገ እንዳለና ስለሆነም ህዝቡ የተጀመረውን ልማት፣ ዴሞክራሲና ሰላም እንዲቀጥል ያለው ፍላጎት ከፍተኛ መሆኑ፣ ያሉትን የመልካም አስተዳደር ችግሮችንም ቢሆን ሊፈታው የሚችለው ራሱ ኢህአዴግ መሆኑን በመተማመን እንደሆነ በግልፅ ነግሮናል።
አንዳንድ ወገኖች ኢህአዴግና አጋሮቹ ሙሉ በሙሉ በማሸነፍ ሁሉንም ወንበሮች ጠራርገው መያዛቸው ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታውና የመድብለ ፓርቲ ስርአቱን አደጋ ላይ የሚጥል ነው የሚል ስጋት ሲሰነዝሩ ይደመጣሉ። ይህ አባባል አንድም የተቃዋሚዎቹን ማንነት በትክክል አለማወቅ አልያም የመድረኩን ባህሪ በትክክል አለመገንዘብ ሊሆን ይችላል፡፡ ዋናውና መሰረታዊው ጉዳይ ተቃዋሚዎች ጥጋቸውን የያዙት በዴሞክራሲያዊ ምርጫ እስከሆነ ድረስ በአውራ ፓርቲ የሚመራ የተረጋጋ የመድብለ ፓርቲ ስርዓት መዳከም ምክንያት ሊሆን እንደማይችል መደምደም እንችላለን፡፡
የከተማችን የ2007 ምርጫ ውጤት ከ2002 የምርጫ ውጤት የተሻለ እንደሆነ ግልፅ ነው። የምርጫ ሂደቱም ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ፍፁም ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊ በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያተረፈ፣ ተቃዋሚዎች ሳይቀር የአዲስ አበባን የምርጫ ሂደትና ውጤት መሰረት አድርገው ለመተቸት የተቸገሩበት ሲሆን በሂደቱም በውጤቱም ካለፉት ምርጫዎች የተሻለና አንዳንድ ከራሳችን የምንወስዳቸው ትምህርቶች እንደተጠበቀ ሆኖ በዋና ዋና መመዘኛዎች ሲታይ እንከን የለሽ ምርጫ ነበር ማለት ይቻላል።
 
 - ክፍተቶቻችንን በግልፅ እንድንለይ ያስቻለ 
   ምርጫ
 
አብዛኛው መራጭ ምርጫው ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እና የህግ ልዕልና ተጠብቆ እንዲጠናቀቅ ተደራጅቶ ተንቀሳቅሷል”” በሌላ በኩል ግን አብዛኛው ህዝብና የመንግስት መዋቅር ትኩረታቸውን በምርጫ ላይ ባደረጉበት ሂደት አንዳንድ ግለሰቦች አጋጣሚውን ተጠቅመው ህገ ወጥ ፍላጎታቸውን ለማሟላት ሲሞክሩ ታይተዋል”” ለምሳሌ የመንግስትና የህዝብን መሬት አላግባብ መውረር፣ ህገ ወጥ ግንባታን ህጋዊ ለማድረግ  ጫና ማድረግና የመሳሰሉት ምልክቶች ታይተዋል። እነዚህን ምልክቶች ግን በተነፃፃሪ የጥቂት ሰዎች ዝንባሌና ተግባር ስለሆኑ ለጊዜው አቆይተን በአብዛኛው ህዝብ ለተሰሩ ጥሩ ነገሮች አውቅና ሰጥቶ መስተካከል አለባቸው ብሎ የሰነዘራቸው ክፍተቶች የነበሩ ቢሆንም ይህ መራጭ ግን ድምፁ ለኢህአዴግ የሰጠ ነው፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ለተቃዋሚዎች ድምፁን የሰጠ አለ”” ተቃዋሚዎች ድምፅ ለምን አገኙ ምክንያቱ ምንድን ነው? በቀጣይ ምን ትምህርት እንወስዳለን? ብለን ማየት ይገባናል፡፡ አንደኛው ምክንያት የመልካም አስተዳደርና አገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ጎላ ብሎ የታየባቸውና በሚፈለገው ደረጃ ባለመቅረፋችን ቅር የተሰኙ ዜጎች፣ ከልማቱ ተጠቃሚ ያልሆኑ ወገኖች  መኖራቸውና የልማቱ ባለቤት አድርገን ማንቀሳቀስ ባለመቻላችን ቅር የተሰኘ መራጭ ቁጥሩ ቀላል አለመሆኑ፣ የአካባቢ ልማት ጥያቄዎች ማለትም ኮብልስቶንና የውስጥ ለውስጥ መንገድ ያልተዳረሰባቸው አካባቢዎች፣ የጎረፍ ማስወገጃ መሸጋገሪያ ድልድዮችና መከላከያ ግንቦች ጥያቄ አለመመለሳችን፣ የወጣት ማዕከላት ጥያቄና የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ጥያቄ ያልተመለሰላቸው አካባቢዎች፣ በውሃ እጥረት፣ መብራት፣ ትራንስፖርት ችግሮች ቅሬታ ያላቸው ዜጎች የተቃውሞ ድምፃቸውን (Protest vote) የሰጡበት ሁኔታ እንዳለ ማየት ይቻላል።
ሁለተኛ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ ኢህአዴግ እንደሚያሸንፍ ገምተው ነገር ግን የተወሰነ ተቃዋሚ ‹‹ለፓርላማ ድምቀት›› መቀላቀል አለበት በሚል አስተሳሰብ በተለይም የተማረ ከሚባለው የህብረተሰብ ክፍል በግልፅ በግል ሚዲያዎችም ጭምር ሲራመድ የነበረና እኛም እንደ አንድ አደገኛና አሳሳች ዝንባሌን ለይተን ዝንባሌውን ለማስተካከል የተንቀሳቀሰንበት ሁኔታ ስለነበር ተቃዋሚዎች ድምፅ ያገኙበት አንድ ምክንያት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል።
ሶስተኛው እና ትልቁ ምክንያት ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርአታችንን ከመሰረቱ የማይቀበሉና የሚቃወሙ የኪራይ ሰብሳቢ ሃይል መሰረት የሆኑ ያለፈው ስርአት ናፋቂዎችና ተስፈኞች የትምክህት፣ የጠባብነትና የአክራሪነት አስተሳሰብ አቀንቃኞች በድምር የሚወክላቸው ኪራይ ሰብሳቢ ሃይል ወደ ስልጣን እንዲመጣ የሚፈልጉ፣ በህገ ወጥ መንገድ ፍላጎታቸውን ለማሟላት የተንቀሳቀሱ ጥቅማቸው የተነካባቸው፣ ለስርአታችን በተለያየ ምክንያት ከባድ ጥላቻ ያላቸው  ቁጥራቸው ምን ያህል ነው የሚለውን ትተን አነሰም በዛም ለተቃዋሚ ድምፃቸውን መስጠታቸው ሌላ እውነታ ነው፡፡ በድምር ተቃዋሚዎች አሁን ላገኙት ድምፅ የነበረው ተፅእኖ ብቻ ሳይሆን በቀጣይም ጊዜ የሚጠብቅ አደገኛ ሃይል መሆኑን ተገንዝበን ፋታ ሳንሰጥ ጠንክረን መስራት ይኖርብናል።